የካህናት ኃላፊነትና የምእመናን ድርሻ

ጌታችንና መድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ፲ ላይ “ኖላዊ ኄር ቸር እረኛ እኔ ነኝ” ሲል አስተምሯል። በዚህ የወንጌል ክፍል ጌታችን ስለአመጣጡ – ትንቢት ተነገሮለት፣ ሱባዔ ተቆጥሮለት፣ የባህርይ አባቱ እግዚአብሔር አብ መስክሮለት የመጣ መሆኑን፣ የመጣውም ለምኅረትና ለቤዛነት መሆኑን ፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ ለፍጥረቱ /ለበጎች/ ምእመን የሚራራ ቸር ጠባቂ መሆኑን አስተምሮበታል። ትምህርቱ ጥልቅ መንፈሳዊ መልእክት ያለውና በተለይም የካህናትን /የአገልጋዮችን/ ኃላፊነት በሚገባ የሚያስገዘብ በመሆኑ በቤተ ክርስቲያናችን ኤጲስ ቆጶሳትና ቀሳውስት ሲሾሙ የሚተረጎም እንደሆነ ከቅዱስ ድሜጥሮስ ሹመት ጋር ተያይዞ በሚተረከው ታሪክ ላይ ተጠቅሶ ይገኛል።
ጌታችን የአዳም ልጆች ሁሉሞት ሰልጥኖባቸው፣ በዲያቢሎስ አገዛዝ ስር ሆነው፣ በገቢረ ኃጢኣት ተይዘው ሲቅበዘበዙ ሞትን ለመደምሰስ፣ ከዲያቢሎስ አገዛዝ ነጻ ለማውጣትና በጎች የተባሉ ምእመናንን በለመለመች መስክ በቤተ ክርስቲያን በማሰማራት የሕይወት ውሃ የተባለ ቃሉን ለመመገብ ነው። ይህንንም ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ፤ በመገረፉ ቁስል ተፈወሳችሁ። እንደ በጎች ትቅበዘበዙ ነበርና፥ አሁን ግን ወደ ነፍሳችሁ እረኛና ጠባቂ ተመልሳችኋል።” (፩ጴጥ ፪፡ ፳፬-፳፭) በማለት ገልጾታል።
መድኃኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ትንቢት የተነገረለት ቸር ጠባቂ መሆኑን አስቀድሞ በልዑለ ቃል ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ተነግሯል። “ እነሆ፥ ጌታ እግዚአብሔር እንደ ኃያል ይመጣል ክንዱም ስለ እርሱ ይገዛል፤ እነሆ፥ ዋጋው ከእርሱ ጋር ደመወዙም በፊቱ ነው። መንጋውን እንደ እረኛ ያሰማራል፥ ጠቦቶቹን በክንዱ ሰብስቦ በብብቱ ይሸከማል፥ የሚያጠቡትንም በቀስታ ይመራል።” (ኢሳ ፵፣፲-፲፩) እውነትም እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጥረቱን በቸርነቱ የሚመግብ፣ የፈጠረውን ፍጥረት ድካም የሚረዳ፣ በኃጢአትና በቀቢጸ ተስፋ የወደቁትን በርኅራኄና በፍቅር የሚያሰማራ ቸር ጠባቂ ነው። ቸር ጠባቂነቱ የተረጋገጠውም ሕጉን ጥሶ፣ አምላክነትን ሽቶ፣ ከገነት ለተባረረው ለአዳምና ልጆቹ /ለበጎቹ/ ነፍሱን አሳልፎ በመስጠቱ ነው።
የካህናት ሹመት
ለቤዛ ዓለምና ለአርአያነት የመጣው ጌታ በዘመነ ሥጋዌው ካከናወናቸው ተግባራት አንዱ በደሙ የዋጃቸውን ምእመናንን የሚጠብቁና የሚያሰማሩ ካህናትን መሾም ነው። ሐዋርያት በአንብሮተ እድ (እጅ በመጫን) ሲሾሙና የመንግሥተ ሰማያት መክፈቻ ቁልፍ /ሥልጣን/ ሲሰጣቸው በተግባር ጌታችን ያስተማረውን የእረኝነት ተግባር ይወጡ ዘንድ ነው። ካህናት አባግዐ ክርስቶስ ምእመናንን በአጸደ ቤተ ክርስቲያን እንዲያሰማሩ ሲሾሙ የተሰጧቸው አደራዎች (የተጣሉባቸው ግዴታዎች)፣ ይህንን ግዴታ ለመፈጸም የተሰጣቸው ሥልጣን ከተጠያቂነት ጋር እንደሆን በቅዱሳት መጻሕፍት ተዘርዝሯል። እነዚህን ከዚህ በታች በጥቂቱ ለመመልከት እንሞክር።
የካህናት ሥልጣን
በሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ አንጻር ለካህናት የተሰጠው ሰማያዊ ስልጣን “የመንግሥተ ሰማያትንም መክፈቻዎች እሰጥሃለሁ፤ በምድር የምታስረው ሁሉ በሰማያት የታሰረ ይሆናል፥ በምድርም የምትፈታው ሁሉ በሰማያት የተፈታ ይሆናል።” (ማቴ ፲፮᎓፲፱፣ ማቴ ፲፰᎓፲፰) እንዲሁም “ ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል።” (ዮሐ ፳፣፳፫) የሚል ጽኑ ሥልጣን ነው። ይህን የመሰለ ከምድር እስከ ሰማይ የሚዘልቅ ሥልጣን የትኛውም ምድራዊ ኃይል የለውም። እያንዳንዱ ካህን የዚህ ሥልጣን ባለቤት መሆኑ የሚያስገርምና የሚያስፈራም ነው። አስገራሚነቱ እግዚአብሔር ሥጋ ለባሽ ለሆነ እና ለራሱ እንኳ ከሥጋ ፍቃድና ከኃጢኣት ጋር ገና እየታገለ ለሚኖር ለደካማው የሰው ልጅ ይህን ያህል ሥልጣን መሰጠቱ ሲሆን አስፈሪነቱ ደግሞ ይህ ኃላፊነት ከተጠያቂነት ጋር የተሰጠ መሆኑን ስንረዳ ነው።
የካህናት ኃላፊነት
ካህናት ዐርዓያ ክህነት ያላቸው፤በእወቀት የተካኑ፣በስነ ልቦና ዝግጁ የሆኑ፣ ከእግዚአብሐር ጋር ያላቸው ግንኙነት ያልተቋረጠ፣ በመንፈስ የጎለመሱ፣እግዚአብሔር የሰጣቸውን ኃላፊነት አክብረው የሚወጡ ሊሆኑ ይገባል፡፡
በሐዲስ ኪዳን ያሉ ካህናት ዋነኛ ኃላፊነት “ጠባቂነት” እንደሆነ ጌታችን ከትንሣኤው በኋላ ለቅዱስ ጴጥሮስ ሦስት ጊዜ ደጋግሞ “ የዩና ልጅ ስምዖን ትወደኛለህን? “ በማለት ከጠየቀው በኋላ “ ግልገሎቼን ጠብቅ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ፣ በጎቼን አሠማራ” በማለቱ ታውቋል። በትንቢተ ሕዝቅኤል ምዕራፍ ፴፬ ላይ ስለእረኝነት የተነገረውን ቃል በሚገባ የሚያነብ ካህን የእረኝነት ኃላፊነትና ተግባር ምን መሆን እንዳለበት ይረዳል። እንኳንስ ሰማያዊ ሥልጣን የተሰጠው ካህን ህዝቡን የማስተዳደር ምድራዊ ሥልጣንና ኃላፊነት የተሰጣቸው ምድራዊያን ነገሥታት በዚህ የመጽሐፍ ክፍል የተጠቀሱትን ኃላፊነቶች እንዳሉባቸው ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ።በዚህ የትንቢት መጽሐፍ የተጠቀሱትን የእረኞች ኃላፊነት አንጻር የሐዲስ ኪዳን ካህናት ኃላፊነት ምን እንደሆነ ለመመልከት እንሞክር።
ሀ) በጎችን በለመለመ መስክ ማሰማራት
የካህናት ተቀዳሚ ተልዕኮ ምእመናን ለምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን ሱታፌ ማብቃት ነው። ካህኑ ከምእመናን ልደት እስከ እረፍታቸው ድረስ በየደረጃው የሚያስፈልጋቸውን አገልግሎት በመስጠት በጥምቀት የሥላሴን ልጅነት፣ በቅብዐ ሜሮን የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ፣ ለአካለ መጠን ሲደርሱ በተክሊሉ የትዳር ህይወታቸውን በመባረክ፣ በኃጢኣት ሲወድቁ በንሰሐ ሳሙና በማጠብ፣ ሲታመሙ በጸሎተ ቀንዲል ፈውስን በመስጠት፣ በየጊዜው በጸሎተ ቅዳሴ በሚያቀርበው መስዋዕት ህዝቡን ከእግዚአብሔር ጋር በማስታረቅ፣ ወተት የሆነ ቃሉን በመመገብ በክርስቲያናዊ ሕይወት በማጽናት ለሥጋ ወደሙ በማብቃት ለሰማያዊው ርስት ያዘጋጃቸዋል። ይህንን ለማድረግ ደግሞ እያንዳንዱን በግ (ምእመን) በስም ማወቅና መለየት፣ ሳያሰልሱ መከታተል፣ ካለምንም ሌላ ተጨማሪ ጥቅም ሊቀርባቸውና ሊከታተላቸው፣ የሚመገቡትም ቃለ እግዚአብሔር እንክርዳድ ያልተቀላቀለበት ንጹሕ መሆኑን ማረጋገጥ ይኖርበታል። ምክንያቱም የነፍስና የስጋ ጠባቂ ተደርጎ ተሾሟልና፡፡ ምእመናን “እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፥ የሚያሳጣኝም የለም። በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፤ በዕረፍት ውኃ ዘንድ ይመራኛል።” (መዝ ፳፪፡ ፩ -፪) ማለት የሚችሉትና የእግዚአብሔርን ቸርነት ሊረዱ የሚችሉት አዕይንተ እግዚአብሔር በተባሉ ካህናት በሚገባ ሲጠበቁና ቃሉን በአግባቡ ሲመገቡ ነው።
ለ) የደከመውን ማጽናት
በጎች ምእመናን በዚህ ዓለም ሃሳብና ውጣ ውረድ ሕሊናቸው ደክሞ፣ ሰውነታቸው ዝሎ ሕገ እግዚአብሔርን ሊዘነጉና ብሎም ወደ ክፋትና አምልኮ ጣዖት ሊሳቡ ይችላሉ፡ በዚህ ወቅት የካህኑ ተግባር በደከሙት መፍረድ ሳይሆን በቃለ እግዚአብሔር በማጽናት “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ። ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ፥ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና፥ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜም ቀሊል ነውና።” (ማቴ ፲፩፡ ፳፰- ፴) የሚል አምላክ እንዳላቸው በማስታወስ ወደ አምልኮተ እግዚአብሔርና ገቢረ ጽድቅ መመለስ ሊሆን ይገባል።
ሐ) የታመመውን ማከም
በጎች ምእመናን በደዌ ሥጋ በደዌ ነፍስ ሲጠቁ ካህኑ ሊለያቸው አይገባም። ደዌ ሥጋ ያገኛቸውን ልጆቹን በጸሎት፣ በጠበል ከመፈወስ ጀምሮ ለሥጋቸው በሚያስፈልጋቸው ሁሉ ሊከታተላቸው ይገባል። በ”ማይድን” ሥጋዊ በሽታ ተይዘው ለቀቢጸ ተስፋ የተዳረጉትን በቅርብ እየተገኘ በማጽናናት መንፈሳዊ ፈውስን የሚሰጥ አምላክ እንዳለ በማስተማር ማጽናናት እና ሰማያዊና ዘላለማዊ ሕይወት እንዳለ ማመላከት ይገባዋል። ከዚህም ሌላ በጎች ምእመናን በጥርጣሬ፣ በዓለማዊ ፍልስፍና፣ በኑፋቄ እና በክህደት ተይዘው ሊታመሙ ይችላሉ። በእነዚህ ደዌዎች የተያዙትንም በጎች ደዌ ሥጋ ከያዛቸው በበለጠ ጥንቃቄና በመንፈሳዊ ጥበብ “ማከም” ይገባል። ካህኑ ማንም ወዶና ፈቅዶ እንደማይታመም አውቆ በፍጹም ሀዘኔታ፣ በየዋሀት መንፈስና በመንፈሳዊ ጥበብ ከጾምና ጸሎት ጋር በደዌ ነፍስ የተያዙትን በጎች ማከም መቻል አለበት። ለካህኑ ዋጋ የሚያሰጠው የሳቱትንና የደከሙትን ተንከባክቦ ለንሰሓ ማብቃት እንጂ አውግዞ መለየት ሊሆን አይገባውም ምንም እንኳንበክህደት በኑፋቄ የታመሙትን መክሮ ዘክሮ የማይመለሱና ሌሎችን የማያስቱ ሆኖ ሲገኝ አውግዞ መለየቱ የግድ መሆኑ የማይቀር ቢሆንም “ወንድሞቼ ሆይ፥ ከእናንተ ማንም ከእውነት ቢስት አንዱም ቢመልሰው፥ ኃጢአተኛን ከተሳሳተበት መንገድ የሚመልሰው ነፍሱን ከሞት እንዲያድን፥ የኃጢአትንም ብዛት እንዲሸፍን ይወቅ” እንዲል። (ያዕ ፭፡ ፲፱_-፳)። ቅዱስ ይሁዳም በመልእክቱ “ አንዳንዶች ተከራካሪዎችንም ውቀሱ፥ አንዳንዶችንም ከእሳት ነጥቃችሁ አድኑ፥ አንዳንዶችንም በሥጋ የረከሰውን ልብስ እንኳ እየጠላችሁ በፍርሃት ማሩ።” (ይሁዳ ፳፪- ፳፫) በማለት የክርስቲያኖች በተለይም የካህናት ድርሻ በኑፋቄና በክህደት ትምህርት የተነጠቁትን ማዳን ጭምር መሆኑን አስገንዝቦናል።
መ) የተሰበረውን መጠገን
የምንኖርባት ዓለም በተለያዩ ተፈጠሮአዊና ሰው ሠራሽ ችግሮች ምክንያትን፣ በተጥባበ ሥጋ ብዛት፣ በሃይማኖት ባልተገራ ምድራዊ ፍልስፍና፣ በዘመናዊነት ስም በማኅበረሰቡ ላይ በተጫኑ አስጨናቂ የኑሮ ዘዬዎች ምክንያት… ወዘተ ከባለ ጸጋውም ከደሃውም ሕይወት የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ የሆነው ደስታ የራቀበት በመሆኑ የብዙ ምእመናን ልብ በሐዘን የተሰበረ ነው። በመንፈሳዊ ሕይወት ለመጽናት የሚሞክሩትን ጭምር ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንዳስጠነቀቀው ዲያብሎስ እንደሚያገሳ አንበሳ ዙሪያቸውን እየዞረ ያስጨንቃቸዋል “ በመጠን ኑሩ ንቁም፥ ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና” (፩ ጴጥ ፭፡ ፰፡) እንዲል። እነዚህን በሐዘን ወስጥ ያሉ እና በስነ ልቦና የተጎዱ ምእመናንን ካህኑ በመንፈሳዊ ጥበብና በቃለ እግዚአብሔር ማጽናት አለበት። ካህኑ በተለይም ልዩ ችግር ያለባቸውን ልጆቹን በመንከባከብ ከበጎቹ መካከል ሰባራዋን፣ አንካሳዋን ጠቦት በጥንቃቄና በቀስታ እንዲያሰማራ ሲያስፈልግም በእቅፉ የሚሸከማትን መልካም እረኛ ሊመስል ይገባል።
ሠ) የባዘነውን መመለስ
በቤተ ክርስቲያናችን በስፋት እንደሚታየው ብዙ ምእመናን የቤተ ክርስቲያን ልጅነታቸውን ባይተዉም ወደ ኑፋቄና ክህደት ባይገቡም ከሕገ እግዚአብሔርና ከምክረ ካህን ተለየተው በፍጹም ዓለማዊ ኑሮ ካላመኑት ባልተለየ ሕይወት እየተመላለሱ ይኖራሉ። ካህኑ ኃላፊነት ያለበት ለእነዚህ በአፍኣ ላሉ ምእመናን ጭምር በመሆኑ ወደ በረት/ ቤተ ክርስቲያን በመጡት ምእመናን ብዛት ሊዘነጋ አይገባውም። ካህናት ትኩረት ሊሰጡና በትጋት ሊሠሩበት የሚገባው ጉዳይ ይህ ነው ። የጸጋ ግምጃ ቤት ከሆነች ከቤተ ክርስቲያን ተለይተው የዲያብሎስ መጫወቻ ለሆኑ ጥሙቃን ክርስቲያኖች ካህኑ ሊያዝንላቸው ይገባል።
ረ) የጠፋውን መፈለግ
ጌታችን በአንቀጸ አባግዕ ካስተማራቸው ትምህርቶች አንዱ “ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምጼንም ይሰማሉ፥ አንድ መንጋም ይሆናሉ እረኛውም አንድ።” (ዮሐ ፲፡ ፲፮) ። ሕዝብና አህዛብን አንድ ያደረገ ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ የቤዛነት ሥራውን የሠራው ዓለም ሁሉ በእርሱ እንዲያምንና የዘላለም ሕይወት እንዲያገኝ ነው። (ዮሐ ፫- ፲፮):: ስለሆነም ካህናት ለልጅነት ተጠርተው ነገር ግን የእግዚአብሔር ልጆች እንደሆኑ ያልተነገራቸውንየጠፉ የተባሉትን በማስተማርና በማጥመቅ ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር የመመለስ መንፈሳዊ ግዴታ አለባቸው። በተለይ ከሀገር ወጭ ያሉ ካህናት ተቀዳሚ ተግባራቸው ወንጌልን ላላመኑት ማድረስ በመሆኑሄዱበትን ሀገር ባህልና ቋንቋ መሳሪያ አድረገው ለማገልገል መዘጋጀት አለባቸው።
የምእመናን ድርሻ
ካህናት አባግዐ እግዚአብሔር ምእመናንን በመጠበቅ ረገድ ያለባቸው ኃላፊነት ከብዙ በጥቂቱ ከዚህ በላይ ተዘርዝሯል። ካህናቱ ይህን ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ከተጠባቂዎቹ ምእመናንም የሚጠበቅ ነገር አለ። ካህናቱ የራሳቸውን እና የቤተሰቦቻቸውን ኑሮ ለማሟላት ከምእመናኑ ባልተናነሰ እየደከሙ ያለባቸውን የክህነት ኃላፊነት እንዲወጡ መጠበቅ አግባብ አይደለም። በመሆኑም ካህናቱ ተረጋግተው የተጣለባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ ምእመናን በኑሮአቸው ሊደግፏቸው ይገባል። ከዚህም በተጨማሪ ምእመናን በምክረ ካህን፣ በፍቃደ ካህን ለመኖር የወሰኑና ካህኑ በሚመራቸው መንገድ ለመጓዝ ፍቃደኛ መሆን አለባቸው እንጂ ለእረኝነት የሚያስቸግሩ ካህኑንም ሆነ ሌሎች ምእመናንን የሚያስቸግሩ እንዳይሆኑ እግዚአብሔር በቃሉ እንዲህ ሲል ይመክራል፤
“ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። እናንተም መንጋዬ ሆይ፥ እነሆ፥ በበግና በበግ መካከል፥ በአውራ በግና በአውራ ፍየልም መካከል፥ እፈርዳለሁ። የቀረውን ማሰማርያችሁን በእግራችሁ የረገጣችሁት፥ በመልካሙ ማሰማርያ መሰማራታችሁ ባይበቃችሁ ነውን? የቀረውንስ ውኃ በእግራችሁ ያደፈረሳችሁት፥ ጥሩውን ውኃ መጠጣታችሁ ባይበቃችሁ ነውን? በጎቼም በእግራችሁ በረገጣችሁት ይሰማራሉ በእግራችሁም ያደፈረሳችሁትን ይጠጣሉ። ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላቸዋል። እነሆ፥ እኔ በወፈሩት በጎችና በከሱት በጎች መካከል እፈርዳለሁ። እስክትበትኑአቸው ድረስ በእንቢያና በትከሻ ስለምትገፉአቸው የደከሙትንም ሁሉ በቀንዳችሁ ስለምትወጉአቸው፥፤ ስለዚህ መንጋዬን አድናለሁ፥ ከእንግዲህ ወዲህም ንጥቂያ አይሆኑም፤ በበግና በበግ መካከልም እፈርዳለሁ።” (ሕዝ. ፴፬: ፲፯- ፳፪) ይላልና ቃሉ ለእረኛችን ከተመቸኝ በለመለመ መስክ እናድራለን፡፡ከእረኛችን ከራቅንና ካልተመቸን በተኩላ /መናፍቅ/ዲቢሎስ እንበላለን፡፡

ማጠቃለያ
በምድራዊው አስተዳደር ባለሥልጣናት በተወሰነና በታወቀ የሕግ ገደብ የተሰጣቸውን ኃላፊነት ይወጣሉ። በተሰጣቸው የሥልጣን ገደብ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ከተወጡ ይመሰገናሉ። ይሸለማሉ። ያለበለዚያም ይወቀሳሉ፤ይከሰሳሉ። በጎች የተባሉ ምእመናን እንዲጠብቁ ሰማያዊ ሥልጣንን የተቀበሉ ካህናትም ከግል ሕይወታቸው በተጨማሪ በተሰጣቸው የክህነት ሥልጣን ምን እንደሰሩበት በሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ይጠየቃሉ። በመሆኑም ካህናት የተሰጣቸውን ኃላፊነት በአግባቡ በመወጣት ለምእመናን ምሳሌና አርአያ በመሆን ከላይ የተዘረዘሩትን ኃላፊነቶች መወጣታቸውን በየጊዜው ራስቸውን መመርመር ይኖርባቸዋል። ምእመናንም ቸሩ እረኛ መድኃኔዓለም በዳግም ምጽኣቱ በቀኙ ከሚያቆማቸው በበጎች ከተመሰሉ ማኅበረ ጻድቃን ለመደመር በምክረ ካህን፣ በፍቃደ ካህን በመኖር ሕገ እግዚአብሔርን በመኖር ልንጸና ይገባል። ሁላችንም ኃላፊነታችንን በአግባቡ ተወጥተን የሰማያዊ ክብር ተካፋዮች እንድንሆን የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሁሉ ተራዳኢነት አይለየን

ስለምን ጾምን፥ አንተም አልተመለከትኸንም? /ኢሳ. ፶፰፥፫/

በቀሲስ ስንታየሁ አባተ

በኢሳያስ ዘመን የነበሩ እስራኤላውያን የተናገሩት ቃል ነው። እስራኤላውያን የሚጾሟቸው ብዙ አጽዋማት ነበሯቸው። ለምሳሌ ያህልም ብናይ በሳምንት ሁለት ጊዜ በሳምንት ሁለት ቀን ይጾሙ እንደነበር በሉቃ. ፲፰፥፲፪ ላይ ያለው ቃል ያስረዳል። ማክሰኞና ሐሙስ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ወደ ደብረ ሲና የወጣበትና ከዚያ የወረደበት ዕለት ለማሰብ እስራኤላውያን በሳምንት ሁለት ቀኖች ይጾሙ ነበር። በነቢዩ በዘካርያስ ትንቢትም ላይ እግዚአብሔር እስራኤላውያንን እንዲህ ብሎ አዝዟቸዋል «የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔር ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ፦ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ Read more

በዓለ ግዝረት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

በዓለ ግዝረት

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅድመ ዓለም በህሊና ያሰበውን፤ ድኅረ ዓለም በነቢያት ያናገረውን ለመፈጸም ሰው ሆነ፣ ሥጋ ለበሰ፤ ሕግ ጠባያዊን ሕግ መጽሐፋዊን እየፈጸመ በጥቂቱ አደገ። ሕግ ጠባያዊ፤ አበ፣ እመ ማለት፣ ለዘመድ መታዘዝ፣ በየጥቂቱ ማደግ ነው። “ወልህቀ በበኅቅ እንዘይትኤዘዝ ለአዝማዲሁ ወለይእቲ እሙ” እንዲል። ሕግ መጽሐፋዊ በስምንት ቀን ቤተ ግዝረት በአርባ ቀን ዕጉለ ርግብ ዘውገ ማዕነቅ ይዞ ቤተ መቅደስ መግባት የመሳሰሉት ናቸው፤ በማለት የመጻሕፍተ ሐዲስ ኪዳን ሊቃውንት በሐዲስ ኪዳን ትርጓሜ መግቢያ ላይ ያመሰጥራሉ፣ ያስተምራሉ።

ቅዱስ ሉቃስ በጻፈው የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ወንጌል ምዕራፍ 1 ቁጥር 59 ላይ ዘግቦልን እንደምናገኘው፤ በዘመነ ብሉይ ወንድ ልጅ በተወለደ በስምንተኛው ቀን ሲገረዝ ስም ይወጣለት ነበር።በመሆኑም ግዝረት የሥጋ ሸለፈት መቆረጥን ያመለክታል።

የግዝረት ሥርዓት ዝም ብሎ የመጣ ሳይሆን እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠው የቃል ኪዳኑ ምልክት ነው። ዘፍ17 ፤ 7-14 በሙሴ የመሪነት ዘመንም ለእስራኤል ህዝብ ምልክትና መለያ ነበር።ዘፀ 12፤43 ፈሪሳውያን ግን ከአብርሃም የመጣ መሆኑን ሳይረዱ በሙሴ እንደተሰጠ ሕጋዊና ሕዝባዊ ምልክት አድርገው ያምኑ ነበር።የሐዋ 15፤1-5 ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን፤ መጀመሪያ ራሱ የሰጠው ለአብርሃም እንደነበርና መንፈሳዊ ምልክትም እንደሆነ አስረድቷቸው ነበር።ዮኀ 7፤22።

የሚከተሉት ሦስት ነጥቦች የግዝረት ዋና ዋና ዓላማዎች ናቸው።

  1. እግዚአብሔር የተገረዘውን ሰው ለራሱ መርጧልና አምላኩ ነው፤ ዘፍ 17፤8
  2. የተገረዙት የእግዚአብሔር ህዝቦች ናቸውና ክፋትንም ከህይወታቸው ማስወገድ አለባቸው፤ ዘጸ 10፤16
  3. እግዚአብሔር በእምነት ስለተቀበላቸው የጽድቃቸው መሠረት ነው፤ ሮሜ 4፤11

ሆኖም በሐዲስ ኪዳን ሥርዓት ሣይሆን፤ የሚያድነው የእግዚአብሔር ህግ መሆኑን ቅዱስ ጳውሎስ ያብራራል።ሮሜ 2፤25 ዋናው ነገር የሥጋ ሸለፈት መገረዝ ሳይሆን የልብ መለወጥና በእግዚአብሔር ማመን ሕጉንም መፈጸም ነው፣ ሲል ቅዱስ ጳውሎስ ምዕመናኑን በመንፈስ የተገረዙ መሆናቸውንም ጨምሮ አብራርቷል።ፊሊጵ 3፤30 በተለይም ህዝብና አህዛብ ማለትም ትንቢት የተነገረላቸው፣ ተስፋ የተነገራቸው እስራኤላውያን እና ከአህዛብ ወገን የመጡት ሁለቱም የክርስትና አማኞች በግዝረት ምክንያት ያስነሱትን አለመግባባት አስመልክቶ በጻፈው መልእክቱ በሐዲስ ኪዳን ዘመን ጥምቀት በግዝረት ፋንታ መተካቱን ያስረዳል።ቆላ 2፤11 ግዝረትም አሁን አይጠቅምም ይለናል። ገላ 5፤6።

ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግዝረት ስንመለስ ደግሞ፤ በመግቢያው እንደተገለጸው ኦሪትና ነቢያትን ልፈጽም እንጂ ልሽራቸው አልመጣሁም እንዳለ፤ ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና እርሱ ራሱ ሥርዓቱን ለመፈጸም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ በስምንተኛው ቀን እናቱ ወደ ቤተ መቅደስ ወስዳው ሊገረዝ በታሰበ ጊዜ በፍጡራን እጅ አልተገረዘም። ምላጩ በገራዡ እጅ እንዳለ ውኃ ሆኖ ተገኝቷል (መጽሐፈ ስንክሳር ጥር ስድስት)።ይህም በመለኮታዊ ኃይሉ ነው። እርሱም በግብር መንፈስ ቅዱስ ተገርዞ ተገኝቷል።ይህንንም ያደረገው ሰውን ንቆ ስርዓቱንም ጠልቶ ሳይሆን ደመ መለኮቱ ያለ ዕለተ ዓርብ የማይፈስ ስለሆነ እርሱ ባወቀ ይህን አደረገ ስሙንም አስቀድሞ በመልአኩ እንደተነገረ ኢየሱስ አሉት። ሉቃ 2፤21

በዚህም ምክንያት ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የግዝረት በዓል በየዓመቱ ጥር 6 ቀን ታከብራለች (መጽሐፈ ስንክሳር ጥር ስድስት)። ስታከብርም በግዝረቱ እለት የተፈጸሙትን ተአምራት በማስተማርና በማሳወቅ ነው።

ለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ምስጋና  ይሁን! አሜን!

ርእሰ ደብር ብርሃኑ አካል

 

በድንግልናሃ ንጹሕ እግዚአብሔር ተወልደ

በድንግልናሃ ንጹሕ እግዚአብሔር ተወልደ

                                ቀሲስ ሳሙኤል ተስፋዬ

በፈቃደ አቡሁ ወረደ፣ኀበ ማርያም ተአንገደ፤ በድንግልናሃ ንጹሕ እግዚአብሔር ተወልደ። በጎለ እንስሳ ተወድየ፣ አምኃ ንግሡ ተወፈየ፤ ወከመ ሕጻናት በከየ፣ እንዘ ይስእል እምአጥባተ እሙ ሲሳየ።

በአባቱ ፈቃድ ወረደ፣ በማርያም ዘንድ፣ እንግዳ ሆነ፣ እግዚአብሔር በንጹሕ ድንግልናዋ ተወለደ። በእንስሳት በረት ተጨመረ፣ የንግሡንም እጅ መንሻ፡ ተቀበለ፣ ከእናቱ ጡቶች ምግብን እየለመነ እንደ ሕጻናት አለቀሰ። (ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ)

 

እግዚአብሔር አምላክ ዓለምንና በውስጧ ያሉትን ፈጠረ ሌሎች ፍጥረታት ለአንክሮ ለተዘክሮ ሲፈጠሩ ሰውና መላእክት ግን ፍቅሩን ክብሩን ይወርሱ ዘንድ ተፈጠሩ፡፡ ዘፍ 1፡1

የሰው ልጅን /አዳምን/ ፈጥሮ የሚያስፈልገውን አዘጋጅቶ፣ ዕውቀትንና ሥልጣን ሰጥቶ፣ በጸጋ አምላክነትን ሾሞ ፣መመሪያ ሰጥቶ፣ በክበር እንዲኖር ፈቀደለት ፡፡ በመጀመሪያው ዕለትና ሰዓት ከተፈጠሩት መላእክት መካከል በክብር ይልቅ የነበረው ሳጥናኤል /የኋላ ስሙ ዲያብሎስ /አምላክነት መሻቱ ተወርዶ ሳለ አዳምንም በተዋረደበት ምኞትና ፍላጎት እንዲወድቅ ክብሩን እንዲያጣ ከአምላኩም እንዲለይ አደረገው፤ እግዚአብሔርን፣ ጸጋውን፣ ሹመቱን፣ አጣ /ኃጥአ/፡፡ ኃጢአት የሚለው ጽንሰ ሐሳብ ከዚህ የተወሰደ ነው፡፡

 

አዳም ከእግዚአብሔር በመለየቱና ክብሩን በማጣቱ ተጸጽቶ ንሰሐ ገባ ፡፡ ሥርየተ ኃጢአት የሚሆን መስዋእትም በማቅረቡ፤ እግዚአብሔር አምላክ ልመናውንና መስዋእቱን ተቀብሎ እርሱንና ዘሩን ለማዳን እንደሚመጣ ቃል ኪዳን ገባለት መዓልትንና ዓመታትን በዚህ ምድር ላይ ሠራሁልህ፡፡ ይኸውም እነርሱ እስኪፈጸሙ ድረስ በምድር ላይ ትኖርና ትመላለስ ዘንድ ነው፡፡ የፈጠረችህና የተላለፍካት ከገነት ያወጣችህና በወደቅህም ጊዜ ያነሳችህ ዳግመኛም አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም የምታድንህ ቃሌን እልክልሃለሁ” /ገድለ አዳም/ ብሎ እግዚአብሔር ለአዳም ነገረው፡፡ አዳምም አምስት ቀን ተኩል የሚለውን ቃል ከእግዚአብሔር በሰማ ጊዜ የእነዚህን ታላላቅ ነገሮች ትርጓሜ ሊያስተውል አልቻለም፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር አምስት ቀን ተኩል ማለት አምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመታት መሆናቸውን ገልጾ አርአያውና አምሳያው ለሆነው አዳም በቸርነቱ ተርጎመለት፡፡ እርሱንና ዘሩን ለማዳን እንደሚመጣ ተስፋ ሰጠው፡፡ ዘፍ 2፡7 ፣ሔኖክ 19 ፡19 ፣ ኩፋሌ 5፡6

 

አዳምም ይህንን ተስፋ ለልጆቹ አስተማራቸው፤ ልጆቹም ተስፋው የሚፈጸምበትን ጊዜ ለማወቅ በፀሐይ፣ በጨረቃና በክዋክብት ዘመናትን እየቆጠሩ “ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንኃለሁ” ያለውን የአዳኝ ጌታ መወለድን ነብያት ትንቢት እየተናገሩ፤ አበውም ሱባኤ እየገቡ ተስፋውን ይጠብቁ ነበር፡፡ ከነሱም ውስጥ:-

  1. ሱባኤ ሔኖክ

ሔኖክ ሱባኤውን ሲቆጥር የነበረው በአበው ትውልድ ሲሆን ሰባቱን መቶ ዓመት አንድ እያለ ቆጥሯል። በስምንተኛው ሱባኤ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚወለድ ትንቢት ተናግሯል። አቆጣጠሩም ከአዳም ጀምሮ ነው። 8×700=5600ዓመት ይሆናል። 5500ዓመተ ዓለም ሲፈጸም ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተወለደ ያጠይቃል። ትንቢቱም እንዲህ ይላል። “ስምንተኛይቱ ሰንበት ጽድቅና ኩነኔ የሚታወቅባት ሰባኤ ናት፡፡ ሰይፍም ለርሰዋ ይሰጣታል፤ ታላቁ ንጉሥ የሚመሰገንበት ቤትም በርሰዋ ይሰራል፡፡ ምሥጋናውም ዘላለማዊ ነው፡፡” ሔኖክ 35፡ 1-2 ክፍል 91 በማለት ሲተነብይ መተርጉማን እንዲህ ይመልሱታል፡፡ ለርሰዋ ሰይፍ ይሰጣታል ማለቱ፤ ጸድቅና ኩነኔ የሚታወቅበት ወንጌል ያን ጊዜ በዓለም ሁሉ ትሰበካለች ማለት ነው፡፡ የታላቁን ንጉሥ ቤት ይሠራል ማለቱ፤ የነገሥታት ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቱስ የሚመሰገንበት ቤተክርስቲያን ትሰራለች ማለት ነው፡፡ ምስጋናውም ዘላለማዊ ነው ማለቱ፤ ሰውና መላእክት በአንድነት ሆነው “ሰብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር” እያሉ ዘወትር ያመሰግናሉ ማለት ሲሆን ስምንተኛይቱ ሰንበት ለክርስቲያኖች የተሰጠችበትን ዕለት ልደት ክርስቶስ ናት ይሏታል፡፡

2. ሱባኤ ዳንኤል

ስለ ጌታችን ሰው መሆን ጊዜ ወስኖ ሱባኤ ቆጥሮ የተናገረው ዳንኤል ነው፡፡ የዳንኤል ሱባኤ የሚቆጠረው በዓመት ነው ፡፡ ዳንኤል 70ው ዘመን በተፈጸመ ጊዜ እጐበኛችኋለሁ ተብሎ በኤርምያስ የተገረውን ትንቢት እያስታወስ ሲጸልይ መልአኩ ቅ/ገብርኤል በሰው አምሳል ተገልጾ እንዲህ ብሎታል፡፡ “እግዚአብሔር ልምናህን ሰምቶሃልና እነግርህ ዘንድ መጥቻለሁ፡፡ አሁንም ነገሩን መርምር ራእዩንም አስተዋሉ ኅጢአት የሚሰረይበትን ቅዱሰ ቅዱሳን ጌታም የባህርይ ክብሩን ገንዘብ የሚያደርግበት ሰባው ሱባኤ ሊደርስ ሊፈጸም ነው ብለህ ወገኖችህን ቅጠራቸው ብሎታል፡፡” /ዳን 9፡22- 25 ኤር 29፡1ዐ/

ሰባ ሱባኤ አራት መቶ ዘጠና ዓመት ነው /7ዐX7= 490/ ይህ ጊዜ ከሚጠት እስከ ክርስቶስ መምጣት ያለው ጊዜ ነው /ትርጓሜ ሕዝ፡4፡6/

  1. ሱባኤ ኤርምያስ

ኤርምያስ ከባቢሎን እንደተመለሰ በፈረሰው ቤተ መቅደስ ውሰጥ ሆኖ ሲጸልይ ሳለ ራዕይ አየ በሦስተኛው ቀንም እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ፡፡ “ፈጣሪያችንን በአንድ ቃሉ አመሰግኑ የአብ የባሕርይ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስን አመስግኑ ከዚህ በኋላ ሰው ሊሆን ሥጋ ሊለብስ ወደዚህ ዓለም ሊመጣ የቀረው 333 ሱባኤ ዕለት ነውና እርሱ ወደዚህ ዓለም ይመጣል፡፡ አሥራ ሁለት ሐዋርያትንም ይመርጣል…፡፡” ተረፈ ኤር 11፤37 ፣38፣42-48፡፡ ኤርምያስ ሱባኤውን የጀመረበትን ትንቢቱን የተናገረበት ራእዩን ያየበት ዘመን ዓለም በተፈጠረ 5054 ዓመት ነው፡፡ ስለዚህ ትንቢቱ ከተነገረበት እስከ ክርስቶስ ልደት ያለው ጊዜ 446 ዓመት ነው፡፡

ይኸውም በኤርምያስ ሱባኤ አንዱ 49ዐ ዕለት ነው መላው ሱባኤ 49ዐX333 = 163,170 ዕለት ሲሆን ወደ ዓመት ሲለወጥ 163, 170÷365 =446 ዓመት

ኤርምያስ ሱባኤውን መቁጥር የጀመረበት ዘመን …….. 5ዐ54 ዓመተ ዓለም

ትንቢቱ ከተነገረበት ዓመት እስከ ክርስቶስ ልደት ……. 446 ዓመት

በተነገረው ትንቢት በተቆጠረው ሱባኤ መሠረት 55ዐዐ ዓመት ሲፈጸም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቱስ መወለዱ በዚህ ይታወቃል፡፡

  1. ዓመተ ዓለም

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱሳት መጻሕፍትን መርምረው ሱባኤያትንና ሰንበታትን አውቀው ከአዳም እስከ ክርስቶስ ያለውን ዘመን ቁጥር 55ዐዐ ዓመት መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡ ይኸውም

ከአዳም አስከ ኖኅ            2256 ዓመት

ከኖኅ እስክ ሙሴ            1588 ዓመት

ከሙሴ እስከ ሰሎሞን        593 ዓመት

ከሰሎሞን አስከ ክርስቶስ   1063 ዓመት

55ዐዐ ዓመት

ጌታችን ኢየሱስ በተነገረው ትንቢት፤ በተቆጠረው ሱባኤ መሠረት /ዓመተ ዓለም፣ ዓመተ ኩነኔ ፣ዓመተ ፍዳ/ አምስት ቀን ተኩል / 55ዐዐ ዓመት/ ሲፈጸም /በእግዚአሔር ዘንድ 1ዐዐዐ ቀን እንደ አንድ ቀን ናት፡፡ 2ኛ ጴጥ. 3፤8 / በ5501 ዓመት ማክሰኞ ታኀሣሥ 29 ቀን ተወለደ፡፡

 

“ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ሥምረቱ ለሰብእ” አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዘመኑ ፍጻሜ /የገባው ቃል ኪዳን፣ የተነገረው ትንቢት፣ የተቆጠረው ሱባዔ/ ሲደርስ ከእመቤታችን ከቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ያጣነውን ልጅነት ሊመልስልን፣ ከተቀማነው ርስት ሊያስገባን፣ የገባንበትን እዳ ሊከፍልልን ተወለደ፡፡

የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት ተወለደ ፡፡ ገላ 4፣4 እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ፤ ቅዱስ ኤፍሬምም “ ቅድስት ድንግል ማርያም ፍጥረታትን ያስገኘ፤ የነገሥታት ንጉሥ የሆነውን ዳግማዊ አዳም ኢየሱስ ክርስቶስን ወለደችልን፡፡ የአሮን በትር ለምልማና ፍሬ አፍርታ ተገኝታ ነበር፤ ይህም ክርስቶስ በድንግልና የመወለዱ ምሳሌ ነው፡፡ እጹብ ድንቅ የሆነ ልደት በዛሬዋ ቀን እውን ሆነ፡፡ ድንግል የሆነችው ቅድስት ማርያም በድንግልና ጌታችንን መድኃኒታችንን ወለደችልን፡፡” ብሏል፡፡

“የእሥራኤል እረኛ ሆይ አድምጥ … በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ ተገለጥ” ብሎ የለመነዉ የዳዊት ልመና በእዉነት ተፈጸመ፡፡ መዝ 70፥1። የእስራኤል እረኛ፤ በእረኞች መካከል በከብቶች በረት ተወለደ። ሉቃ 2፥7፡፡ እረኞች ለእረኛቸው ዘመሩ፤ ላሞች፣ በጎችና አህዮች በበረት የተኛውን ሕፃን በትንፋሻቸው አሟሟቁ። በኦሪት ድንኳን በሙሴ ሕግ መሠረት ለመሥዋዕት ይቀርቡ የነበሩ እንስሳት በልደቱ ደስ ተሰኙ፤ የነርሱን መሥዋዕት የሚያስቀር አማናዊው የእግዚአብሔር በግ ተወልዷልና።

ለሰው ሁሉ ብርሃን የሚሰጥ እግዚአብሔር በጨለማው ዓለማችን ተወለደ። (ዮሐ.1፥9-14) ነቢያትና መምህራን ጠፍተውባት፣ የኃጢአት ጨለማ ዉጧት፣ በድንቁርና ባሕር ውስጥ ሰጥማ በነበረችው የሰው ልጆች ዓለም የእውነት ፀሐይ ወጣ። እነሆ ይህን ይገልጥ ዘንድ መድኅን በእኩለ ሌሊት በጨለማ ተወለደ፤ በተወለደ ጊዜ ግን ክብሩ በዙርያው አበራ። (ሉቃ.2፥8-9)

ለመንግሥቱ ወርቅ ተገበረለት። ኃያል መንግሥቱን ግን በምድር ላይ በትህትና ነበር የገለጣት፤ በከብቶች በረት በመወለድና በአህያ ውርንጭላ ተቀምጦ በመሄድ። (ሉቃ.19፥28-38) የአባታችን የዳዊት መንግሥት ያለልክ ከፍ ከፍ አለች፤ እግዚአብሔር ሰው ሆኖ የዳዊት ልጅ ሆኗልና። ቅዱስ ገብርኤል ቅድስት ድንግል ማርያምን ባበሠራት ጊዜ “እርሱ ታላቅ ይሆናል፣ የልዑል ልጅም ይባላል፤ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፣ በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘላለም ይነግሣል፣ ለመንግሥቱም መጨረሻ የለዉም” ብሎ የተናገረዉ ዛሬ ተፈጸመ፡፡ (ሉቃ.1፥32)፡፡

 

በባሕርይው የፍጥረት ሁሉ ገዥ የሆነዉ የእግዚአብሔር ልጅ ከዳዊት ልጅ ሥጋን ነስቶ ሰዉ በሆነ ጊዜ የአባቱን የዳዊትን ዙፋን እስከ ጽርሐ አርያም ድረስ ከፍ ከፍ አደረጋት። እነሆ ንጉሥ ክርስቶስ በያዕቆብ ቤት (በምእመናን) ላይ ለዘላለም ነገሠ። ለመንግሥቱ የአሕዛብ ነገሥታት ተገዙላት፤ የእግዚአብሔር መንግሥት ናትና ፍጥረታት ሁሉ ይገዙላታል። (ኤር.23፥5)

ለክህነቱ ዕጣን ተሰጠው። ክህነቱም የአበውን እና የሌዋውያንን ክህነት የምትፈጽም የዘላለም ሰማያዊት ሥራው ናት። እነሆ የአብ ሊቀ ካህናት እርሱ የሰውን ባሕርይ ከራሱ ጋር አስማማ። ራሱ ካህን፣ ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ ተቀባይ ሆኖ የፈጸማት የክህነት ሥራው የዘላለም ድኅነትን አስገኘች።

ለሞቱ ከርቤ ቀረበለት። እነሆ እግዚአብሔር ሰው የሆነበት ዋናው ምክንያት በሞቱ ሞትን ድል ለመንሣት ነውና በልደቱ ሞቱ ተሰበከ። ከርቤ ለሞቱ ሲቀርብለት የማይሞተው እርሱ ለሰው ልጆች ሲል የሚሞት ሥጋን እንደለበሰ ታወቀ።

የአሕዛብ ነገሥታት ወርቅ ገበሩለት፤ ምእመናን ደግሞ ጽሩይ፣ ንጹሕ፣ ሰማያዊ የሆነ ልቦናን እና እምነትን ለእርሱ እናቀርባለን። (1ኛ ጴጥ.1፥6) ሰብአ ሰገል ራሱ የፈጠረውን ወርቅ ገበሩለት፤ እኛም በርሱ ጸጋና ሥራ ያገኘነውን ንጹሕና ሰማያዊ እምነታችንን እናቀርብለታለን (ይሁ.3)።

ነገሥታቱ ዕጣን ገበሩለት፤ ምእመናን ደግሞ ቂም በቀል የሌለበትን፣ ከመልካም እና ከንጹሕ ልብ የሚወጣ የምስጋና ጸሎት እናቀርባለን፤ “ጸሎቴን በፊትህ እንደ ዕጣን ተቀበልልኝ፥ እጅ መንሣቴንም እንደ ሠርክ መሥዋዕት ትሁን።” እንዳለ ንጉሥ ዳዊት (መዝ.140፥2) ።

ስለሰው ልጆች ፍቅር ሲል ለሚቀበለው ሞት ከርቤ ገበሩለት፤ ምእመናን ደግሞ ለእግዚአብሔርና ለሰው ልጆች ያለንን ፍቅር ለእርሱ እናቀርባለን። ነገሥታቱ እርሱ ከፈጠረው ከርቤ ወስደው እጅ መንሻ አቀረቡ፡፡ ምእመናን ደግሞ ከእርሱ ከተማርነው፣ ከመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ከተቀበልነው ፍቅር መልሰን ለእርሱ እናቀርባለን። “እርሱ ስለኛ ነፍሱን አሳልፎ ሰጥቷልና በዚህ ፍቅርን አውቀናል፤ እኛም ስለ ወንድሞቻችን ነፍሳችንን አሳልፈን ልንሰጥ ይገባናል፡፡ (1ኛ ዮሐ.3፥16)።”

ነቢዩ ኢሳይያስ “በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን አየ በሞት ጥላ አገርም ለኖሩ ብርሃን ወጣላቸዉ” ብሎ የተናገረዉ ትንቢት ተፈጸመ (ኢሳ.9፥2)። የቅድስናዉ ተራራና ማደሪያው ወደ ሆነች ወደ መንግሥተ ሰማያት ይወስደናል፡፡ በዚች የዘላለም ሃገራችንም የሚያበራልን ፀሐያችን እርሱ ነዉ፡፡ (ራእይ.21፥23)።

እነሆ ሰው የመሆኑ ዜና የሰው ልጆች ሁሉ ደስታ ነው፡፡ “እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፡፡ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና።” የሚል ዜና በሰማያውያን መላእክት ተሰበከ። (ለቃ.2፥11)

የምድር ኃያላን ነገሥታት በከብቶች በረት ውስጥ በጨርቅ ተጠቅልሎ ለተኛው ሕፃን መብዓ አቀረቡ። ንጹሐንና ኃያላን የሚሆኑ የሰማይ መላእክት ደግሞ እግዚአብሔር ለሰው ፍቅር ሲል እንደ ሕፃን ተጠቅልሎ ሲያዩ በታላቅ ትሕትና ከእረኞች ጋር ዘመሩ። (ሉቃ.2፥13)

በዳዊት ከተማ በቤተልሔም ድንቅ ነገር ተደረገ። ዳዊት በወርቅ ያጌጠ የተልባ እግር መጎናጸፊያ የለበሰባት ቤተልሔም የሰማይና የምድር ፈጣሪ በጨርቅ ተጠቅልሎ ተገኘባት። ቤተልሔም ከዳዊት ዘመን አብልጣ ከበረች፤ የእግዚአብሔር ክብር አብርቶባታልና፤ የልዑላን መላእክት ዝማሬ ተሰምቶባታልና። (ሚክ.5፥2)

 

በዚህች ዕለት እግዚአብሔር ወደ ኃጢአተኞች መጣ፤ ስለዚህ ጻድቁ በኃጢአተኞች ላይ አይታበይ፡፡ በዚህች ቀን የሁሉ ጌታ የሆነው እርሱ ወደ ባሮቹ መጣ፤ እናንተ ጌቶች ሆይ እንደ ጌታችን ለአገልጋዮቻችሁ ቸርነትን አድርጉላቸው፡፡ በዚህች ቀን ባለጠጋ የሆነው እርሱ ስለ እኛ ሲል ደሃ ሆነ፡፡ እናንተ ባለጠጎች ሆይ ከማዕዳችሁ ለድሃው አካፍሉ፡፡ በዚህች ቀን እኛ ያላሰብነውን ስጦታ ከጌታ ዘንድ ተቀበልን፤ እኛም ምጽዋትን ለሚጠይቁን ድሆች ቸርነትን እናድርግ፡፡ ከእኛ ይቅርታን ሽተው የመጡትን ይቅር እንበላቸው፡፡ በዛሬዋ ቀን የፍጥረት ጌታ የሆነው እርሱ ከባሕርይው ውጪ የሰውን ተፈጥሮ ገንዘቡ አድርጎ በሥጋ ተገልጦአልና፣ እኛም ወደ ክፉ ፈቃድ የሚወስደንን ዐመፃ ከእኛ ዘንድ አርቀን በአዲስና እርሱ በሰጠን መንፈሳዊ ተፈጥሮ እንኑር፡፡… እኛ በአምላክ ማኅተም እንድንታተም እርሱ አምላክነቱን ከእኛ በነሳው ሥጋ አተመው፡፡ሰው አምላክ ሆነ አምላክ ሰው ሆነ ማለት ነው፡፡

የአምላካችንን የኢየሱስ ክርስቶስን የልደት በዓል ስናከብር ፍቅሩን እያሰብን በኃጢያታችን ምክንያት ከልባችን ያወጣነው ሁሉ ዛሬም በልባችን እንዲወለድ ያስፈልጋል፡፡ “የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ የት አለ?” ማቴ. 2÷1

 

እግዚአብሔር ለምን ሰው ሆነ?

 

ከንጹሕ ባሕርይ ተፈጥሮ የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ በደስታ ይኖር የነበረ ሰው የፈጣሪውን ትዕዛዝ በመተላለፉ ከንጽህና ወጥቶ ኃጢአትን ለበሰ:: ሕይወቱን አስወስዶ ሞትን ተቀበለ:: የእግዚአብሔር ልጅነቱን አስቀርቶ የዲያቢሎስ ምርኮ ሆነ:: ደስታውን አጥቶ ኃዘን አገኘው:: ተጸጽቶ የጥንት ሕይወቱንና ደስታውን ለማግኘት ጥረት ቢያደርግም፤ ንጹህ ባሕርይው ስላደፈበት የሞት ፍርድን ሊያስቀርለት አልቻለም::

ዳግማዊ አዳም የተባለ የፍቅር አምላክ፣ የሁሉ ፈጣሪ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የሞት ፍርድን ሊያስቀር ኃጢአትን ደምስሶ ከሞት ፍርድና ከገሃነም ነጻ ሊያወጣ  ሰው ሆነ፤ ተወለደ:: “እርሱም ኃጢአትን ሊያስወግድ እንደ ተገለጠ ታውቃላችሁ፥ በእርሱም ኃጢአት የለም።” 1ዮሐ 3:5

በዚህም መሰረት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በአምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመተ ዓለም ዘመነ ዮሐንስ መጋቢት ሀያ ዘጠኝ ቀን እሑድ ከቀኑ ሶስት ሰዓት ተጸነሰ:: በአምስት ሺህ አምስት መቶ አንድ ዓመተ ዓለም በዘመነ ማቴዎስ ታኅሣሥ ሃያ ዘጠኝ ማክሰኞ ከሌሊቱ አስር ሰዓት ተወለደ::

 

ገና-ጌና-ገኒን፤ልደት

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበት ቀን በዓል ገና ወይም በዓለ ልደት በመባል ይታወቃል:: ገና የሚለው ቃል ገነወ አመለከ ከሚለው የግእዝ ቃል የተወሰደ ነው:: የጌታችን ልደትም የአምላክ ሰው፤ ሰው አምላክ የመሆን ምሥጢር የተገለጠበት ታላቅና ገናና ስለሆነ ገና ተብሏል:: አምላክ አለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡ ይበልጣል እንዲል ሃይማኖተ አበው::

የገና ጨዋታ

በሃገራችን በኢትዮጵያ የገና በዓል በተለያዩ ዝግጅቶች ደምቆ ይከበራል:: በተለይ በገጠሩ ያገራችን ክፍል ከዚህ በዓል ጋር በተያያዘ አባቶችና እናቶች ክብረ በዓሉን ምክንያት በማድረግ በገና ይደረድራሉ:: ወጣቶችም የገና ጨዋታ ይጫወታሉ:: “በገና” ስሙን ያገኘው በገና በዓል ወቅት የሚደረደር በመሆኑ ነው ሲሉ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ያስተምራሉ:: በሌላም ትውፊት በተለይ በገጠሩ አካባቢ የሚገኙ ወጣቶችና አዛውንቶች የሚጫወቱት የገና ጨዋታ ራሱን የቻለ ባህልና ትውፊት አለው:: የገና ጨዋታ ራሱ በተቆለመመ በትርና ሩር የተባለ ከዛፍ ሥር በተሠራ ክብ እንጨት(ኳስ) እያጎኑ የሚጫወቱት ጨዋታ ነው፡፡

ሰብአ ሰገል በኮከብ እየተመሩ ወደ ቤተልሔም ሲሔዱ “የተወለደው የአይሁድ ንጉስ ወዴት አለ” በማለት ቢጠይቁ ይህንን አስደንጋጭ ጥያቄ የሰማው ንጉሥ ሔሮድስ “እኔ ንጉሥ ሆኜ ሳለሁ ሌላ ንጉሥ እንዴት ይወለዳል” በማለት የተወለደውን ንጉሥ ለመግደል አገልጋዮቹን ከሰብአ ሰገል ጋር ሄደው ቦታውን አይተው እንዲመለሱ ላካቸው፡፡ የሔሮድስ አገልጋዮች ከተቀላቀሉ በኋላ እየመራ ያመጣቸው ኮከብ ጌታ የተወለደበትን ቦታ መምራቱን አቆመ፡፡ ሰብአ ሰገል ተጨንቀው “የኮከቡ እርዳታ ለምን ተለየን” ብለው ሲመረምሩ ከነሱ ዓላማ ውጭ ሌላ ሀሳብና ተንኮል ይዘው የተገኙ ሰዎችን አገኙ፡፡ “በእናንተ ምክንያት የእግዚአብሔርን እርዳታ አጣን”፡፡ ብለው ሦስቱም ነገሥታት(ሰብአ ሰገል) ከአንዱ ወደ አንዱ እየተቀባበሉ በብትር እየመቱ አስወገዷቸው፡፡

ኮከቡም እየመራ ጌታ በተወለደበት ቦታ ቤተልሔም አደረሳቸው ከእረኞችና ከመላእክት ጋራ አመሰገኑት፡፡ እረኞች ጌታ በተወለደ ጊዜ ጨለማ ተሸንፎ አካባቢያቸው በብርሃን ተመልቶ መንፈስ ቅዱስ በገለጸላቸው ምስጢር ከመላእክት ጋራ “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ሥምረቱ ለሰብእ” እያሉ ሲያመስግኑና ሲደሰቱ አድረዋል፡፡ በአሉ እረኞች ክብር ያገኙበት ምስጢር የተገለጠላቸው ስለሆነ በስነ ቃል “በገና ጨዋታ አይቆጡም ጌታ” እየተባለም በጨዋታ እንደሚከበር እንደሆነ አበው ይናገራሉ፡፡

ይህ ትውፊት የገና ጨዋታ እየተባለ ወጣቶች አዛውንቶች በጨዋታ ያከብሩታል፡፡ ራሱ የተቆለመመውና ሩሯን የሚያጎነው በትር የጌታችን ምሳሌ ሲሆን ሩሩ ደግሞ የሳጥናኤል ምሳሌ ነው:: ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ዝቅ አድረጎ የሰውን ሥጋ በመልበስ ወደዚህ ምድር እንደመጣና በሩር የተመሰለውን ሰይጣንን እንደቀጠቀጠው የሚያሳይ ምሥጢር ያለው ጨዋታ ነው::

ሰንበት ዘብርሃን

ሰንበት ዘብርሃን

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

ነአምን ክልኤተ ልደታተ እንዳሉ አባቶቻችን በሃይማኖተ አበው፤ ቅድመ ዓለም ከእግዚአብሔር አብ ያለ እናት፣ አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ የተወለደ፣ ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው የአብ አካላዊ ቃል ፤ ድኀረ ዓለም ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ያለ አባት፣ መለወጥ ሳያገኛት ዘር ምክንያት ሳይሆን፣ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ሰው የሆነ ፤ ወልደ እግዚአብሔር በመለኮቱ ወልደ ማርያም በትስብእቱ ፤ የሚባል ጌታ በተዋሕዶ ከበረ ብለን የቀናች የአባቶቻችን ሃይማኖታቸው ተዋሕዶን እንመሰክራለን፡፡

ስንዱዋ እመቤት ቤተክርስቲያናችን ወራትን እና ዘመናትን ከፍላ ነገረ ሃይማኖትን ታስተምራለች።አባቶቻችንም የወራቱንና የቀናቱን  የሰንበታቱንም ምስጢር በማገናዘብ የመጽሐፍ ቅዱስን ምንባባት ከቅዱስ ያሬድ መዝሙር ጋር በማዛመድ ግጻዌ የሚባልን መጽሐፍ ሰርተውልናል።

መዝሙር ዘብርሃን

በግጻዌ ዘሰናብት ከታኅሣሥ ፲፬  እስከ ታኅሣሥ ፳  ባሉት ቀናት ውስጥ ያለውን ሰንበት ብርሃን እንደሚባልና መዝሙሩም “ዘብርሃን አቅዲሙ ነገረ በኦሪት”የሚለው እንደሆነ አባቶቻችን ሠርተውልናል፡፡

ይህም የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ነገረ ሥጋዌን ነገረ ድኅነትን በውስጡ የያዘ ነው። ቅዱስ ያሬድ እንደ ንብ ነው፤ንብ ከመልካም አበባ ሁሉ እንዲቀስም ቅዱስ ያሬድም ከኦሪቱ ከነቢያቱ ከሐዲሳቱ እየጠቀሰ መጥኖ ማር የሆነውን ቃለ እግዚአብሔር አዘጋጅቶልናል፡፡

“ዘብርሃን አቅዲሙ ነገረ በኦሪት ከመ ይመጽእ ወልድ በስብሐት ዘይዜንዋ ለጽዮን ቃለ ትፍሥሕት”

ቃለ ትፍሥሕት የደስታ ቃልን አንድም ደስ የሚያሰኝ የምስጋና ቃልን፣ ለጽዮን ለሕዝበ ፳ኤል  የሚነግራት፣ ወልድ በክብር በምስጋና ለተዋሕዶ ለድኅነተ ዓለም ፣ ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም እንደሚመጣ  አስቀድሞ በኦሪት ተነገረ ይለናል ሊቁ ቅዱስ ያሬድ፡፡

አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው እንደሚሆንና እኛን እንደሚያድነን አስቀድሞ በኦሪት የተነገረውን ሲያስታውሰን ነው ፡፡ ለአብነትም  “አዳም መልካምንና ክፉን ለማወቅ ከእኛ እንዳንዱ ሆነ” ዘፍ  ፫፥፳፪ ተብሎ የተነገረው የወልደ እግዚአብሔርን ሰው መሆን የሚያሳይ ነው፡፡

“ወካዕበ ይቤ በአፈ ዳዊት ቡሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር ”

ዳግመኛ ምስክርነቱ የታመነ አምላክ እንደልቤ ብሎ ባከበረው በቅዱስ ዳዊት አንደበት “በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው” መዝ ፻፲፯፥፳፮ አለ ይለናል ሊቁ  ቅዱስ ያሬድ፡፡ በስመ እግዚአብሔር፦ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ በእግዚአብሔር ስም ፤በስምዐ እግዚአብሔር፦ እግዚአብሔር አብ መስክሮለት የመጣ ወልደ እግዚአብሔር ጌታ የባሕርይ አምላክ ነው፡፡ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትን በአፈ ዳዊት እያለ ትንቢቱን ምስክርነቱን ያነሳዋል ፡፡ አባቶቻችንም ከልደተ ዳዊት እስከ ፍልሰተ ባቢሎን ያለውን ፲፬ ትውልድ በሰንበት ዘብርሃን ያስቡታል፡፡

“ብርሃን ዘመጽአ ውስተ ዓለም ዘያበርህ ላዕለ ጻድቃን”

ቅዱስ ያሬድ ወልደ እግዚአብሔርን ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም የመጣው ብርሃን ዘበአማን፤  የዚህ ዓለም ጠፈር ደፈር የማይከለክለው መዓልትና ሌሊት የማይፈራረቅበት እውነተኛ ብርሃን፤ ለጻድቃን የሚያበራ ብሎ ይገልጠዋል፡፡ ይህም ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌል የመሰከረው ሊቃውንቱ እነ ቅዱስ ኤፍሬም በእመቤታችን ውዳሴ ላይ ያመሰጠሩት ነው፡፡

“መርዓዊሃ ለቤተ ክርስቲያን”

ቅዱስ ያሬድ ወልደ እግዚአብሔርን የቤተክርስቲያን ሙሽራ ብሎ ይገልጠዋል፡፡አካል የሌለው ራስ እንደሌለ ፥ ሙሽሪት የሌለችውም ሙሽራ የለም ። አካል፥ ሙሽሪት ያላት ቤተክርስቲያንን ሲሆን ራስ፥ ሙሽራ የተባለው ደግሞ ክርስቶስ ነው።ይህንም ቅዱስ ጳውሎስ “ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደ ሆነ እርሱም አካሉን የሚያድን እንደ ሆነ ባል የሚስት ራስ ነውና” ብሎ ገልጦታል ኤፌ ፭፥፳፫

“ይርዳእ ዘተኀጒለ ያስተጋብእ ዝርዋነ መጽአ ኀቤነ”

ከ፻ በጎች መካከል የጠፋውን አዳምንና ልጆቹን ይረዳ ይፈልግ ዘንድ፣ የተበተኑትን ይሰበስብ ዘንድ ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም ወደ እኛ መጣ ፡፡

ምስባክ ዘብርሃን መዝ ፵፪፥፫


‹‹ፈኑ ብርሃነከ ወጽድቀከ

እማንቱ ይምርሓኒ ወይሰዳኒ ደብረ መቅደስከ

ወውስተ አብያቲከ እግዚኦ  ››

 

ፈኑ ብርሃነከ ወጽድቀከ

 

  • (ብርሃነከ) ብርሃን የተባለ ወልድን (ወጽድቅከ) መንፈስቅዱስን ላክልኝ
  • ብርሃነ ረድኤትህን አንድም ዮሴዕ ዘሩባቤልን ቂሮስ ዳርዮስን ላክልኝ
  • (ብርሃነከ) ሐዋርያትን (ወጽድቅከ) ሰብአ አርድእትን ላክልኝ
  • (ብርሃነከ) መስቀልን (ወጽድቅከ) ቀኖትን  ላክልኝ
  • (ብርሃነከ) ሥጋውን (ወጽድቅከ) ደሙን ላክልኝ

 

እማንቱ ይምርሓኒ ወይሰዳኒ ደብረ መቅደስከ

 

ብርሃን  የተባለ ወልደ እግዚአብሔርን በሐዋርያት በሰብአ አርድእት ትምህርት አምነን ሥጋውን ደሙን ተቀብለን መከራ መስቀሉን አስበን ወደመንግስቱ እንገባለንና እሊህ መርተው መመስገኛህ ወደምትሆን ወደ ኢየሩሳሌም ይውሰዱኝ ዘንድ ይላል ኅሩይ ቅዱስ ዳዊት


ወውስተ አብያቲከ እግዚኦ

እነሱ መርተው ወደ ገነት ወደ መንግሥተ ሰማያት ያግቡኝ።አብያት ብሎ መንግስተ ሰማያትን በብዙ ቁጥር ይናገራል።በብዙ ወገን በድንግልና፣ በሰማዕትነት፣ በብሕትውና አንድም በብዙ ማዕረግ በ፴፣ በ፷፣ በ፻ የምትወረስ ስለሆነ ነው።አንድም በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ እንዳለው በብዙ ተናገረ

በብርሃን የሚነበቡ ምንባባት

 

በሰንበት ዘብርሃን የሚነበቡ ምንባባት በዕለቱ መዝሙር ‹‹ዘብርሃን አቅዲሙ ነገረ በኦሪት›› ብርሃን ዘበአማን የተባለው እውነተኛው የዓለም ብርሃን ክርስቶስ ለሰው ልጆች ድኅነት ወደዚህ ዓለም እንደሚመጣ በኦሪት በነቢያት አስቀድሞ መነገሩን የሚያበስሩ የልደተ ክርስቶስን ዋዜማ የሚያስታውሱ ናቸው

 

    • ሮሜ  ፲፫ ፲፩ ፡ ፲፬ ‹‹ከእንቅልፍ የምትነሡበት ሰዓት አሁን እንደ ደረሰ ዘመኑን እወቁ፤ ካመንንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን ዛሬ ወደ እኛ ቀርቦአልና።ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል። እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር እንልበስ።በቀን እንደምንሆን በአገባብ እንመላለስ፤ በዘፈንና በስካር አይሁን፥ በዝሙትና በመዳራት አይሁን፥ በክርክርና በቅናት አይሁን፤ነገር ግን ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን ልበሱት፤ ምኞቱንም እንዲፈጽም ለሥጋ አታስቡ።….››

 

  • ፩ኛ ዮሐ ፩ ፥ ፩፡፲ ‹ስለ ሕይወት ቃል ከመጀመሪያው የነበረውንና የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን የተመለከትነውንም እጆቻችንም የዳሰሱትን እናወራለን፤ሕይወትም ተገለጠ አይተንማል እንመሰክርማለን፥ ከአብ ዘንድ የነበረውንም ለእኛም የተገለጠውን የዘላለምን ሕይወት እናወራላችኋለን፤እናንተ ደግሞ ከእኛ ጋር ኅብረት እንዲኖራችሁ ያየነውንና የሰማነውን ለእናንተ ደግሞ እናወራላችኋለን። ኅብረታችንም ከአባት ጋር ከልጁም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ነው።ደስታችሁም እንዲፈጸም ይህን እንጽፍላችኋለን።ከእርሱም የሰማናት ለእናንተም የምናወራላችሁ መልእክት። እግዚአብሔር ብርሃን ነው ጨለማም በእርሱ ዘንድ ከቶ የለም የምትል ይህች ናት።ከእርሱ ጋር ኅብረት አለን ብንል በጨለማም ብንመላለስ እንዋሻለን እውነትንም አናደርግም፤ነገር ግን እርሱ በብርሃን እንዳለ በብርሃን ብንመላለስ ለእያንዳንዳችን ኅብረት አለን፥ የልጁም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል።ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፥ እውነትም በእኛ ውስጥ የለም።በኃጢአታችን ብንናዘዝ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው።ኃጢአትን አላደረግንም ብንል ሐሰተኛ እናደርገዋለን ቃሉም በእኛ ውስጥ የለም።››
  • የሐዋ ፳፮ ፥፲፪ ፡ ፲፱ ‹‹ስለዚህም ነገር ከካህናት አለቆች ሥልጣንና ትእዛዝ ተቀብዬ ወደ ደማስቆ ስሄድ፥ንጉሥ ሆይ፥ በመንገድ ሳለሁ እኩል ቀን ሲሆን በዙሪያዬና ከእኔ ጋር በሄዱት ዙሪያ ከፀሐይ ብሩህነት የበለጠ ብርሃን ከሰማይ ሲበራ አየሁ

 

ሁላችንም በምድር ላይ በወደቅን ጊዜ። ሳውል ሳውል፥ ስለ ምን ታሳድደኛለህ የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል የሚል ድምፅ በዕብራይስጥ ቋንቋ ሲናገረኝ ሰማሁ።እኔም  ጌታ ሆይ፥ ማንነህ አልሁ እርሱም አለኝ። አንተ የምታሳድደኝ እኔ ኢየሱስ ነኝ።ነገር ግን ተነሣና በእግርህ ቁም፤ ስለዚህ እኔን ባየህበት ነገር ለአንተም በምታይበት ነገር አገልጋይና ምስክር ትሆን ዘንድ ልሾምህ ታይቼልሃለሁና።የኃጢአትንም ስርየት በእኔም በማመን በተቀደሱት መካከል ርስትን ያገኙ ዘንድ፥ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሰይጣንም ሥልጣን ወደ እግዚአብሔር ዘወር እንዲሉ ዓይናቸውን ትከፍት ዘንድ፥ ከሕዝቡና ወደ እነርሱ ከምልክህ ከአሕዛብ አድንሃለሁ።ንጉሥ አግሪጳ ሆይ፥ ስለዚህ ከሰማይ የታየኝን ራእይ እምቢ አላልሁም››

 

ወንጌል ዘብርሃን ዮሐ ፩፥፩ – ፲፱



‹‹በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ።ይህ በመጀመሪያው በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ።ሁሉ በእርሱ ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም።በእርሱ ሕይወት ነበረች፥ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች።

ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም።ከእግዚአብሔር የተላከ ስሙ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤ሁሉ በእርሱ በኩል እንዲያምኑ ይህ ስለ ብርሃን ይመሰክር ዘንድ ለምስክር መጣ።ስለ ብርሃን ሊመሰክር መጣ እንጂ፥ እርሱ ብርሃን አልነበረም።ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበር።በዓለም ነበረ፥ ዓለሙም በእርሱ ሆነ፥ ዓለሙም አላወቀውም።የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም።ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም።ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን።

ዮሐንስ ስለ እርሱ መሰከረ እንዲህም ብሎ ጮኸ። ከእኔ በኋላ የሚመጣው እርሱ ከእኔ በፊት ነበረና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፤ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነበረ።እኛ ሁላችን ከሙላቱ ተቀብለን በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጥቶናልና ሕግ በሙሴ ተሰጥቶ ነበርና፤ጸጋና እውነት ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ሆነ። መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው።አይሁድም አንተ ማን ነህ ብለው ይጠይቁት ዘንድ ከኢየሩሳሌም ካህናትንና ሌዋውያንን በላኩበት ጊዜ፥ የዮሐንስ ምስክርነት ይህ ነው››

 

በትርጓሜ ወንጌል አባቶቻችን ይህን ስለ መለኮታዊ የሕይወት ቃልና ስለ ዮሐንስ መላክ የሚያትተውን ምንባብ በሰፊው አምልተው አመስጥረው ጽፈው አስቀምጠውልናል።

  • በቅድምና ስለነበረው ቃል ሲያብራሩ፦ ተጠመቀ ለማለት ተወለደ ማለት ጥንቱ ነው፤ተወለደ ለማለት ተፀነሰ ማለት ጥንቱ ነው፤ተፀነሰ ለማለት በቅድምና ነበረ ማለት ጥንቱ ነው።ያ ቃል ከስነፍጥረት አስቀድሞ የነበረ እግዚአብሔር ወልድ እንደሆነ ሲያስረዳም ያም ቃል ስጋ ሆነ ብሎ ያመጣዋል።ልብ እስትንፍስ ቀድመውት ወደኋላ የሚገኝ ቃል የለምና ቅድስት ሥላሴ አባት በመሆን አብ ወልድን አይቅድመውም አይበልጠውም፤ ወልድም መንፈስቅዱስን አይበልጠውም አይቀድመውም ፤ሦስቱ ስም አንዱ እግዚአብሔር ነው ብሎ አባ ሕርያቆስ እንደተናገረ አሐቲ ቅድምናሆሙ ለሥላሴ ወዕሩያን እሙንቱ በቅድምና እንዲል የቅድስት ሥላሴ ቅድምና አንድ የሆነ የተካከለ ቅድምና ነው።
  • ስለ ዮሐንስ መላክ ሲያብራሩ፦መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የብርሃንን ነገር ይመሰክር ዘንድ የመጣ እንጂ እራሱ ብርሃን አይደለም፤ሰው ሁሉ ብርሃን በተባለ ክርስቶስ ያምን ዘንድ የሚናገር፤በጨለማ በድንቁርና፣ በቀቢጽ ተስፋ በሞት ጥላ ውስጥ ሁሉ ለሚኖር ዓለም ፣ ዕውቀትን የሚገልጥ ጨለማን የሚያርቅ፣ ምትን ድል አድርጎ ተስፋ መንግስተ ሰማያትን የሚሰጥ  መሆኑን መስክሯል።

 

ማቴ ፭፥፲፮ ‹‹መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ››በጎ ሥራችሁን አይተው ሰማያዊ አባታችሁን እንደነርሱ  አርአያ የሚሆኑ የትሩፋት አበጋዝ ያስነሳልን አምላካችን ብለው እንዲያመሰግኑት ብርሃን በጎ ሥራችሁ ይገለጥ ብሎ ቅዱስ መጽሐፍ ያስተምረናል።ብርሃን ዘበአማን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃን ዕውቀትን በጎ ምግባርን ያድለን በብርሃን የምንመላለስ የብርሃን ልጆች ያድርገን  ወንድማችን የምናሰናክል ሳይሆን ለሌላው አርአያ የምንሆን ያድርገን።

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በኩረ ፍሥሐ ቀሲስ ኃይለኢየሱስ ተመስገን

 

ዘመነ ስብከት

በኩረ ፍሥሐ ቀሲስ ኃይለኢየሱስ ተመስገን

ዘመነ ስብከት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

ከሁሉ አስቀድሞ ሃይማኖትን መመስከር እንዲገባ ቅድመ ዓለም ከእግዚአብሔር አብ ያለ እናት፣ አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ የተወለደ፣ ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው አካላዊ ቃል ፤ ድኀረ ዓለም ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ያለ አባት፣ መለወጥ ሳያገኛት ዘር ምክንያት ሳይሆን፣ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ሰው የሆነ ፤ ወልደ እግዚአብሔር በመለኮቱ ወልደ ማርያም በትስብእቱ ፤ የሚባል ጌታ በተዋሕዶ ከበረ ብለን የቀናች የአባቶቻችን ሃይማኖታቸው ተዋሕዶን እንመሰክራለን፡፡

ስንዱዋ እመቤት ቤተክርስቲያናችን ወራትን እና ዘመናትን ከፍላ ነገረ ሃይማኖትን ታስተምራለች።አባቶቻችንም የወራቱንና የቀናቱን  የሰንበታቱንም ምስጢር በማገናዘብ የመጽሐፍ ቅዱስን ምንባባት ከቅዱስ ያሬድ መዝሙር ጋር በማዛመድ ግጻዌ የሚባልን መጽሐፍ ሰርተውልናል።

አባቶቻችን ሊቃውንት ከኅዳር ፮  እስከ  ስብከት  ያለውን ንዑስ ዘመን  ዘመነ አስተምህሮ ይሉታል፡፡ ስብከት የሚውለው ከታኅሣሥ ፯ እስከ  ፲፫  ባሉት ቀናት ውስጥ በሚውለው እሁድ በመሆኑ ፤ ዘመነ አስተምህሮ ዝቅ ብሎ  ከኅዳር ፮ እስከ ታኅሣሥ ፯  ወይም ከፍ ብሎ  ከኅዳር ፮  እስከ  ታኅሣሥ ፲፫ ያለውን ጊዜ ያጠቃልላል፡፡

ዘመነ አስተምህሮ ከዘመነ ስብከት መቅደሙ እግዚአብሔር አዳምን ይቅር እንዳለው ለማጠየቅ ሲሆን፣ ከዘመነ አስተምህሮ ቀጥሎ ዘመነ ስብከት መባሉ ደግሞ አዳምን ይቅር ያለው ንጉሠ ሰማይ ወምድር እግዚአብሔር አምላክ ሰው ሁኖ የሚወለድበት ዘመን እንደ ደረሰ ለማጠየቅ ነው፡፡

 

ስብከት ኢይወርዱ ታኅሣሥ ሰባት ሲሆን ኢየዐርጉ ደግሞ ታኅሣሥ ዐሥራ ሦስት ስለሆነ ከታኅሣሥ ሰባት እስከ ታኅሣሥ ዐሥራ ሦስት ባለው ይመላለሳል ፡፡

በዚህም ዕለተ ሰንበት  ሙሴ በኦሪት፥ ነቢያትም ስለ እርሱ ስለጻፉለት ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ስጋዌ ትንቢቱን አውቆ ያናገረ ምሳሌውን ያስመሰለ ነቢያት አስቀድመው ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም እንደሚመጣ ሰው ሆኖ  እንደሚያድነን ትንቢት መናገራቸውን ሱባኤ መቁጠራቸውን የሚነገርበት የሚሰበክበት በመሆኑ ስብከት ይባላል።

አባቶቻችን ስብከት የሚውልበትን ቀን የሚያሰሉት በወርኀ ታኅሣሥ መባቻ ፣ በነቢየ እግዚአብሔር በኤልያስ ክበረ በዓል ነው፡፡ የባህረ ሐሳቡን ትምህርት በመያዝ በቀላሉ ለማስታወስ ጥንተ ቀመርን ወይም የዕለታት ተውሳክን በመጠቀም ማስላት እንችላለን፡፡

ጥንተ ቀመርን በመጠቀም ስናሰላ

 

ስብከት ታኅሣሥ ፲፫ የሚሆነው ኤልያስ(ታኅሣሥ መባቻ)  በጥንተ ቀመር (በዕለተ ማክሰኞ)  የዋለ እንደሆነ ነው፡፡በዚህም መሰረት፦

  1. ታኅሣሥ 1 ማክሰኞ ከዋለ ፣ ስብከት ታኅሣሥ 13 ቀን ይውላል፡፡
    2. ታኅሣሥ 1 ረቡዕ ከዋለ ፣  ስብከት ታኅሣሥ 12 ቀን ይውላል፡፡
    3. ታኅሣሥ 1 ሐሙስ ከዋለ፣ ስብከት ታኅሣሥ 11 ቀን ይውላል፡፡
    4. ታኅሣሥ 1 አርብ ከዋለ ፣ስብከት ታኅሣሥ 10 ቀን ይውላል፡፡
    5. ታኅሣሥ 1 ቅዳሜ ከዋለ፣ ስብከት ታኅሣሥ 9 ቀን ይውላል፡፡
    6. ታኅሣሥ 1 እሑድ ከዋለ፣ ስብከት ታኅሣሥ 8 ቀን ይውላል፡፡

7.ታኅሣሥ 1 ሰኞ ከዋለ፣ ስብከት ታኅሣሥ 7 ቀን ይውላል፡፡

የዕለታት ተውሳክን በመጠቀም ስናሰላ

 

የዕለታት ተውሳክ በቅዳሜ ይጀምራል እርሱም ፰ ነው ፡፡ ቅዳሜ(8) ፣ እሁድ(7) ፣  ሰኞ(6) ፣ ማክሰኞ(5) ፣ ረቡዕ(4) ፣ ሃሙስ(3) ፣ ዓርብ(2)

በዚህም መሰረት፦

1.ታኅሣሥ 1 ቅዳሜ ከዋለ፣ ስብከት (1+8=9) ታኅሣሥ 9  ቀን ይውላል፡፡

2.ታኅሣሥ 1 እሑድ ከዋለ፣ ስብከት (1+7=8) ታኅሣሥ 8  ቀን ይውላል፡፡
3.ታኅሣሥ 1 ሰኞ ከዋለ፣ ስብከት (1+6=7) ታኅሣሥ 7 ቀን ይውላል፡፡
4.ታኅሣሥ 1 ማክሰኞ ከዋለ ፣ ስብከት (1+5=6 ይሆናል።ሰባት ስላልሞላ ሌላ ሳምንት ይፈልጋል ስለዚህ  6+7=13 ) ታኅሣሥ 13 ቀን ይውላል፡፡
5. ታኅሣሥ 1 ረቡዕ ከዋለ ፣  ስብከት (1+4+7=12) ታኅሣሥ 12 ቀን ይውላል፡፡
6. ታኅሣሥ 1 ሐሙስ ከዋለ፣ ስብከት(1+3+7=11)  ታኅሣሥ 11 ቀን ይውላል፡፡
7. ታኅሣሥ 1 አርብ ከዋለ ፣ስብከት (1+2+7) ታኅሣሥ 10 ቀን ይውላል፡፡

 

ምስባክ ዘስብከት መዝ ፻፵፫፥፯


‹‹ፈኑ እዴከ እምአርያም ፤

አድኅነኒ ወባልሐኒ እማይ ብዙኅ፤

ወእምእዴሆሙ ለደቂቀ  ነኪር ። ››

 

በስብከት (ከታኅሣሥ ፯ እስከ  ፲፫  ባሉት ቀናት ውስጥ በሚውለው እሁድ) ነቢያት የጌታን ሥጋዌ ማስተማራቸው ይነገርበታል ፡፡ አዳም ዕፀ በለስን በልቶ ልጅነቱን ካጣ ከገነት ከወጣ በኋላ ‹‹እግዚአብሔርን ያህል ጌታ ገነትን ያህል ቦታ በኃጢአቴ ምክንያት አጣው›› እያለ ሲያዝን ጌታ ኀዘኑን አይቶ ጸሎቱን ሰምቶ ‹‹ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅ ተወልጄ አድንኃለው›› ብሎ ተስፋ ሰጥቶታል፡፡  ከእሱ በኋላ የተነሱ ነቢያት በግዝረታቸው፣ በመስዋዕታቸው መዳን የማይቻላቸው ቢሆን ለአዳም በሰጠው ተስፋ ከሰማያት ወርዶ፣ ከድንግል ተወልዶ፣ በሕማሙ በሞቱ ያድናቸው ዘንድ ‹‹ፈኑ እዴከ እምአርያም  እጅህን ከአርያም ላክ አድነኝም››  እያሉ ተማጽነውታል፡፡

 

ፈኑ እዴከ እምአርያም

 

እድ መዝራዕት የሚባል ልጅህን በሥጋ ላክ አንድም ረድኤትህን ከአርያም ላክ፤ኢየሱስ ክርስቶስን እዱ መዝራዕቱ ለአብ ይለዋል።የሰው ኀይሉ በክንዱ እንዲታወቅ የአብም ኀይሉ በውልድ ይታወቃልና አንድም ክንድ ከአካል ሳይለይ የወደቀውን ዕቃ አንስቶ ይመለሳል እርሱም ከአብ አንድነት ሳይለይ አዳምን ያድናልና አድኗልና እንድም በክንድ የራቀውን ያቀርቡበታል የቀረበውን ያርቁበታል በርሱም ጻድቃንን ንዑ ኀቤየ ብሎ ያቀርብባታል ኃጥአንን ሑሩ እምኔየ ብሎ ያርቅበታልና ነው።

 

አድኅነኒ ወባልሐኒ እማይ ብዙኅ

 

በሥልጣንህ ከብዙ መከራ ከብዙ ጦር አድነኝ ፤አንድም በልጅህ ከፍትወታት እኩያት ከኀጣውእ ከፍዳ ከመከራ ነፍስ ፈጽመህ አድነኝ።

ወእምእዴሆሙ ለደቂቀ  ነኪር

 

ከዲያቢሎስ ወገኖች ሥልጣን አድነኝ አንድም ከባዕድ ልጆች እጅ አድነኝ።
ሀብተ ትንቢት የተሰጠው ቅዱስ ዳዊት የጌታን ልደት በተስፍ ተመልክቶ ከዚህም በተጨማሪ ሌሎችን ትንቢቶች ተናግሯል።

 

በስብከት የሚነበቡ ምንባባት

 

በስብከት የሚነበቡ ምንባባት በዕለቱ መዝሙር ‹‹ወልዶ መድኅነ ንሰብክ ዘእምቅድመ ዓለም ሀሎ…››ከዓለም በፊት የነበረውንና መድኃኒት የሆነውን ወልድን እንሰብካለን በሚለው የቅዱስ ያሬድ ዜማ ተስማምተው የተዘጋጁ ናቸው።

 

በዚህ ዕለት የሚነበቡት ምንባባት፥ ነቢያት ሱባኤ እየገቡ ምሥጢር እየተገለፀላቸው ስለ ነገረ ሥጋዌው ትንቢትና በብዙ ምሳሌ መናገራቸውን እንዲሁም   ተስፋ ትንቢታቸው በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መፈጸሙን የሚያስረዱ ናቸው።

 

    • ዕብ ፩፥፩-፲፬ ‹‹ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ አይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ ፥ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን፤እርሱም የክብሩ መንጸባረቅና የባሕርዩ ምሳሌ ሆኖ፥ ሁሉን በስልጣኑ ቃል እየደገፈ፥ ኃጢአታችንን በራሱ ካነጻ በኋላ በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀመጠ….››

 

  • ፪ኛ ጴጥ ፫ ፥ ፩፡፲ ‹‹ወዳጆች ሆይ፥ አሁን የምጽፍላችሁ መልእክት ይህች ሁለተኛይቱ ናት። በቅዱሳን ነቢያትም ቀድሞ የተባለውን ቃል በሐዋርያቶቻችሁም ያገኛችኋትን የጌታንና የመድኃኒትን ትእዛዝ እንድታስቡ በሁለቱ እያሳሰብኋችሁ ቅን ልቡናችሁን አነቃቃለሁ።በመጨረሻው ዘመን እንደ ራሳቸው ምኞት የሚመላለሱ ዘባቾች በመዘበት እንዲመጡ ይህን በፊት እወቁ፤እነርሱም  የመምጣቱ የተስፋ ቃል ወዴት ነው፧ አባቶች ከሞቱባት ጊዜ፥ ከፍጥረት መጀመሪያ ይዞ ሁሉ እንዳለ ይኖራልና ይላሉ።….››

 

  • የሐዋ ፫ ፥ ፲፯ ፡ ፳፮ ‹‹አሁንም፥ ወንድሞቼ ሆይ፥ እናንተ እንደ አለቆቻችሁ ደግሞ ባለማወቅ እንዳደረጋችሁት አውቄአለሁ፤እግዚአብሔር ግን ክርስቶስ መከራ እንዲቀበል አስቀድሞ በነቢያት ሁሉ አፍ የተናገረውን እንዲሁ ፈጸመው።እንግዲህ ከጌታ ፊት የመጽናናት ዘመን እንድትመጣላችሁ አስቀድሞም ለእናንተ የመረጠውን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዲልክላችሁ፥ ኃጢአታችሁ ይደመሰስ ዘንድ ንስሐ ግቡ ተመለሱም።እግዚአብሔር ከጥንት ጀምሮ በቅዱሳን ነቢያቱ አፍ የተናገረው፥ ነገር ሁሉ እስከሚታደስበት ዘመን ድረስ ሰማይ ይቀበለው ዘንድ ይገባልና።ሙሴም ለአባቶች። ጌታ አምላክ እኔን እንዳስነሣኝ ነቢይን ከወንድሞቻችሁ ያስነሣላችኋል፤ በሚነግራችሁ ሁሉ እርሱን ስሙት።ያንም ነቢይ የማትሰማው ነፍስ ሁሉ ከሕዝብ ተለይታ ትጠፋለች አለ።ሁለተኛም ከሳሙኤል ጀምሮ ከእርሱም በኋላ የተናገሩት ነቢያት ሁሉ ደግሞ ስለዚህ ወራት ተናገሩ።እናንተ የነቢያት ልጆችና እግዚአብሔር ለአብርሃም። በዘርህ የምድር ወገኖች ሁሉ ይባረካሉ ብሎ፥ ከአባቶቻችን ጋር ያደረገው የኪዳን ልጆች ናችሁ።ለእናንተ አስቀድሞ እግዚአብሔር ብላቴናውን አስነሥቶ፥ እያንዳንዳችሁን ከክፋታችሁ እየመለሰ ይባርካችሁ ዘንድ፥ ሰደደው።››

 

 

 

ወንጌል ዘስብከት ዮሐ ፩፥፵፬፡፶፪

 

‹‹በነገው ኢየሱስ ወደ ገሊላ ሊወጣ ወደደ፥ ፊልጶስንም አገኘና ተከተለኝ አለው። ፊልጶስም ከእንድርያስና ከጴጥሮስ ከተማ ከቤተ ሳይዳ ነበረ። ፊልጶስ ናትናኤልን አግኝቶ ሙሴ በሕግ ነቢያትም ስለ እርሱ የጻፉትን የዮሴፍን ልጅ የናዝሬቱን ኢየሱስን አግኝተነዋል አለው።

ናትናኤልም ከናዝሬት መልካም ነገር ሊወጣ ይችላልን አለው። ፊልጶስ መጥተህ እይ አለው።ኢየሱስ ናትናኤልን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ ስለ እርሱ ተንኰል የሌለበት በእውነት የእስራኤል ሰው እነሆ አለ።

ናትናኤልም ከወዴት ታውቀኛለህ አለው። ኢየሱስም መልሶ ፊልጶስ ሳይጠራህ፥ ከበለስ በታች ሳለህ፥ አየሁህ አለው።

ናትናኤልም መልሶ መምህር ሆይ፥ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፤ አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህ አለው።

ኢየሱስም መልሶ ከበለስ በታች አየሁህ ስላልሁህ አመንህን ከዚህ የሚበልጥ ነገር ታያለህ አለው።እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ አለው።››

 

በዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል  እንደምንረዳው ፊሊጶስ ናትናኤልን እንደጠራውና ፤ናትናኤልን ፊሊጶስ ሳይጠራው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ናትናኤልን  እንደሚያውቀው፤ ስለእርሱም ደግነት መናገሩን እናያለን።

አባቶቻችን ፊሊጶስ ሳይጠራህ በፊት ከበለስ በታች ሳለህ አየሁህ የሚለውን በአንድምታ ትርጓሜ አስቀምጠውልናል

  • በቅትለተ ሕጻናት ሄሮድስ ሕጻናቱን ሲያስፈጅ እናቱ በቀፎ አድርጋ ከበለስ ሥር ሠውራው ነበርና ያንጊዜ ያዳንኩህ እኔ ነኝ ሲል ነው
  • ሰው ገድሎ አስቀብሮ ነበርና አንድም  የጎልማሳ ሚስት ቀምቶ የማይገባ ሥራ ሲሰራ ነበርና አውቅብሀለሁ ሲለው ነው
  • ባለጸጋ ነው ከዚያ ሆኖ ወይፋፍን ሲያስፈትን ፈረስ በቅሎ ሲያሰግር ይውል ነበርና አውቅሀለሁ ሲለው ነው
  • ምሑረ ኦሪት ነው ከዚያ ሆኖ የተነገረው ትንቢት ደረሰ የተቆጠረው ሱባኤ ቀረ እያለ ሲያወጣ ሲያወርድ ይውል ነበርና አውቅልሃለሁ ሲለው ነው።
  • የበለስ ቅጠሉ ሰፊ እንደሆነ ኃጢአት ሰፍናብህ አየሁህ ሲለው ነው።

በዚህም የስብከትና የትምህርት ዕለት ነገረ ሥጋዌው እና የነቢያት ውረድ ተወለድ አድኅነን የሚል ጸሎትና ልመና በሚታሰብበት ሰንበት ፤ ሁላችንም እራሳችን በቃለ እግዚአብሔር መክረን የአምላካችን ውለታ ማሰብ ያስፈልገናል።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ቤተ መቅደስ ገባች

 

በቀናችው መንገድ  በሃይማኖት ጸንተው፣

በቅዱስ ጋብቻ ትእዛዙን አክብረው፣

ምግባር ከሃይማኖት አሰተባብረው  ይዘው፤

ጸሎት ያልተለየው ቅዱስ ሕይወታቸው፣

ኢያቄም ወሐና ልጅ ወልዶ ለመሳም ቢፈቅድም ልባቸው፣

ሳይወልዱ ሳይከብዱ ገፋ ዘመናቸው።

ጸሎታቸው ቢደርስ   ልጅን ቢሰጣቸው፣

ብጽዓት ነውና ከአምላክ ውላቸው

የአምላክ አያት ሆነው ድንግልን ሰጣቸው፡፡

ሐናና ኢያቄም  ከሁሉም ልቀዋል፣

ፈጣሪን የምትወልድ ድንግልን ወልደዋል።

ጸሎት ያልተለየው ቅዱስ ሕይወታቸው፣

የፈጣሪን እናት መውለድ አስቻላቸው።

የሐና የኢያቄም የከበረች ፍሬ፣

ምስጋና እየሰማች ውዳሴ ዝማሬ፣

በቤተ መቅደስ ውስጥ ልትኖር አገልግላ፣

ገባች ቤተ መቅደስ ሦስት ዓመት ስትሞላ።

ሐና ሰጥታት ስትሄድ አድርሳት ከመቅደስ፣

ድንግል ወደ እናቷ ስትሄድ ስትመለስ፣

ዝቅ አለ ፋኑኤል ከሰማይ ወረደ፣

በክንፎቹ ጋርዶ መግቧት ዐረገ።

የሦስት ዓመት ሕፃን ትንሽ ብላቴና፣

የበኩር ልጃቸው የኢያቄም የሐና፡፡

በክንፎቹ ጋርዶ መልአክ የመገባት፣

ቤተ መቅደስ ገባች የአማኑኤል እናት።

ሰማዮችን ቀደህ ምነው ብትወርድ ያለው፣

የኢሣይያስ ስብከት ፍጻሜው ደርሶ ነው።

አምላክን ለመውለድ ቀድማ የታሰበች፣

አሥራ-ሁለት ዓመት ቤተ መቅደስ ኖረች።

ኢያቄም ወሐና እናትና አባትሽ፣

ኅልም አይተው ነበረ ድንግል መጸነስሽ።

ተአምሩ ብዙ ነው እም አምላክ ልደትሽ፣

ቤተ መቅደስ ሆነ ድንግል ሆይ ዕድገትሽ።

ዝናብ የታየብሽ ትንሿ ደመና፣

አንቺ መሶበ ወርቅ ውስጥሽ ያለ መና።

«እንደ ልቤ» ብሎ አምላክ ስም የሰጠው፣

ከእረኝነት መርጦ ንጉሥ ያደረገው፣

በጸጋ ተመልተሽ ቢመለከት ከብረሽ፣

በግርማ በሞገስ ወርቅ ተጎናጽፈሽ፣

በሰማይ በክብር በቀኝ በኩል ቢያይሽ፡

ወትቀውም ንግሥት ብሎ ተቀኘልሽ።

የሁላችን_ተስፋ_የአዳም_የስብከት ቃል፣

የነቢያት ምሥጢር የሲና ሐመልማል፣

የሕዝቅኤል ራእይ የነቢያት ትንቢት፡

ቅኔው ለሰሎሞን መዝሙሩ ለዳዊት።

ተሰምቶ አይጠገብ ውዳሴሽ መብዛቱ፣

ለአባ ሕርያቆስ አንቺ ነሽ ድርሰቱ።

እናታችን ማርያም ጥዑመ ስም ያለሽ፣

ጥዑመ ስም ያለው ክርስቶስን ወልደሽ፣

ዓለም ይባረካል ይኸው እስከ ዛሬ፣

መድኃኒት ነውና ከአንቺ የወጣው ፍሬ።

የነደደው እሳት በሲና ሐመልማል፣

ምሳሌ ለድንግል ምሳሌ ነው ለቃል።

ያንን ነበር ያየው ሙሴ በድንቁ ቀን፣

መለኮት ማደሩን በድንግል ማኅፀን።

አባ ሕርያቆስ ውዳሴሽ በዝቶለት፣

የምስጋናሽ ነገር ምሥጢር ተገልጦለት፣

የክብርሽን ነገር በአድናቆት በማየት፣

ይመሰክር ጀመር በጣፈጠ አንደበት።

እግሩ ከምድር ሳይለቅ ሐሳብ አመጠቀው፣

በደመና ጭኖ የኋሊት ወሰደው።

ያሬድ በዝማሬው ንዑድ ክቡር ያለሽ፣

ድንግል እናታችን የገነት ቁልፍ ነሽ።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር።

አብርሃም_ሰሎሞን።

ክብረ ክህነት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ክብረ ክህነት

ክፍል አንድ፡  አጀማመሩና ሥርዓቱ

ክህነት ተክህነ ካለው የግእዝ ቃል የወጣ፣የተገኘ ቃል ሲሆን አገለገለ ማለት ነው።መሥዋዕት ፣ጸሎት ልመና ወደ እግዚአብሔር እያቀረቡ ሰውና እግዚአብሔርን ማስታረቅ፣ እግዚአብሔር አምላክ ይቅር እንዲል ዘወትር በመሥዋዕቱ ፊት እየቆሙ መጸለይ ምሕረትን ፣ይቅርታን ከእግዚአብሔር ማሰጠት፤ ህዝቡ ደግሞ ኃጢአት እንዳይሠሩ ፣ሕገ እግዚአብሔርን እንዳይተላለፉ መምከር፣ማስተማር፣መገሰጽ መቻል ሲሆን በአጠቃላይ ክህነት ማለት በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የቆመ ምሰሶ፣ መሰላል ወይም ድልድይ ማለት ነው። ሰውና እግዚአብሔር ይገናኙበታልና።

የክህነት አገልግሎት የተጀመረው ዓለም ከመፈጠሩ በፊት ነው።ዓለም የሚለው ቃል በራሱ ብዙ ትርጉም ያለው ሲሆን በአንድ በኩል የሰው ልጅ እራሱ ዓለም ይባላል። ሊቁ ቅዱስ ያሬድ፤ “ኢኃደጋ ለምድር እምቅድመ ዓለም ወእስከ ለዓለም እንበለ ካህናተ ወዲያቆናት…” እግዚአብሔር አምላክ ዓለምን ከመፍጠሩ በፊትም ሆነ ከፈጠረ በሁዋላ ምድርን ያለካህናትና ዲያቆናት አልተዋትም ማለት ነው። በሥነ-ፍጥረት ቅደም ተከተል መሠረት የሰው ልጅ ከመፈጠሩ በፊት ቅዱሳን መላእክት እንደተፈጠሩ እና የክህነት አገልግሎትን እንደጀመሩ እንረዳለን። በመጽሐፈ ቅዳሴም፤ “እምቅድመ ይፍጥር መላእክተ ለቅዳሴ ኢተጸርአ ስብሐተ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ” ሲል መላእክትን እንኳን ለምስጋና ከመፍጠሩ በፊት በአንድነት በሦስትነት መመስገኑ በባህርይው ያልተቋረጠ መሆኑን ነው የሚያስረዳን።

ወደ ሰው ልጅ የክህነት አገልግሎት ስንመጣ ደግሞ በሦስት አበይት ክፍላተ ዘመን መድበን ማየት እንችላለን። በዘመነ ሕገ ልቡና፣ በዘመነ ብሉይ ኪዳን እና በዘመነ ሐዲስ ኪዳን ብለን።

ክህነት በህገ ልቦና፤ የቤተሰብ ክህነት በመባል ይታወቅ ነበር። ምክንያቱም መሥዋዕቱ የሚሰዋው፣ ጸሎቱ የሚጸለየው፣ ልመናው፣ሥርየቱ ስለቤተሰብ ብቻ ስለነበረ ነው። ለዚህም መነሻው አባታችን አዳም ራሱ ሕገ እግዚአብሔርን በመተላለፍ ዕፀ በለስን በልቶ፣ኃጢአት ሠርቶ፣ ከገነት በወጣና ከፈጣሪው በተለየ ጊዜ ንሰሐ ገብቶ፣ መሥዋዕት ሠውቶ፣ ወደፈጣሪው ባመለከተ ጊዜ ንሰሐን የሚቀበል እግዚአብሔር ንስሐውን ተቀብሎ የተስፋውን ቃል ሰጠው። ይህም ቃል “በሐሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እተወለድ እምወለተ ወለትከ…” አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ፤ ህፃን ሆኜ፣ በምድርህ ተመላልሼ፣ በመስቀል ላይ በዕለተ ዐርብ ተሰቅዬ በሞቴ አድንኃለሁ የሚለው ነው። ይህም ቃል በመጽሐፈ ቀሌምንጦስ በመጀመርያው ክፍል የሚገኘው ሲሆን ቅዱስ ያሬድም በድጓው በዜማ እያዋዛ፣ እያቀነባበረ በተደጋጋሚ ሲያመሰጥረው እናገኛለን።

ኢዮብም ምናልባት ልጆቼ እግዚአብሔርን በልባቸው ሰድበው ይሆናል ብሎ ይልክና ይቀድሳቸው ነበር። ኢዮብም ማልዶ ተነስቶ እንደቁጥራቸውም ሁሉ የሚቃጠል መሥዋዕት አቀረበ እንደሁ ኢዮብ ሁልጊዜ ያደርግ ነበር። ኢዮ 1፣ 5። ጻድቁ ኖኅም ከማየ አይህ በሁዋላ መሥዋዕት እንደሠዋ እና እግዚአብሔር የገባለትን ቃል ኪዳን መሐላውንም በቀስተ ደመና ምልክት እንዳጸና ይህችም ቀስተደመና የድንግል ማርያም ምሳሌ መሆኗን ኢትዮጰያዊው ሊቅ አባ ጽጌ ድንግል “ቀስተደመና ማርያም ትዕምርተ ኪዳኑ ለኖኀ ዘእግዚአብሔር ሤመኪ ለተዝካረ ምሕረተ ወፍትህ…” እግዚአብሔር ለዓለም ድኀነት ያቆማት የቀስተደመናዋ ምሳሌ ድንግል ማርያም አንቺ ነሽ፤ እግዚአብሔር ለምሕረትና ለፍርድ ሹሞሻልና ሲል ነው።

አበ ብዙኀን አብርሃም ከሚታወቅባቸው በጎ ሥራዎቹ አንዱ ሁል ጊዜ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት በማቅረቡ ነው።በዚህም ከመሥዋዕት ሁሉ የሚበልጠውን አንድ ልጁን ይስሐቅን ሳይቀር በቆራጥነት ለመሥዋዕት እንዳቀረበ እናያለን። በዚህ ሥራውም የእግዚአብሔር ወዳጅ ተባለ። በሕገ ልቦና ሁሉም አባቶች መሥዋዕት ለማቅረብ ባለድርሻ ቢሆኑም ከዚህ በላይ የተጠቀሱት ምሳሌ ናቸው።እዚህ ላይ ለየት ያለው ሌላው ክህነት የመልከጼዴቅ ክህነት ነው። ይህ የአዲስ ኪዳን ምሳሌ ሲሆን እራሱ መልከጼዴቅም የክርስቶስ ምሳሌ ነው። ከላይ እንደተጠቀሰው የሕገ ልቦና ክኅነት የቤተሰብ ክኅነት የተባለበት ምክንያት መሥዋዕቱ ለራሱና ለቤተሰብ ብቻ እንጂ ሌላውን የሚያካትት መሥዋዕት፣ ጸሎት ልመና ባለመሆኑ ነው። ብዙኃኑን አለማካተቱ ብቻ ሳይሆን የሚያስገኘውም ሥርየት ጊዜያዊ ሥርየት ማለትም ከአባር፣ ከቸነፈርና ከመቅሠፍት የሚያድን ሥጋዊ ድኀነት ብቻ እንጂ ነፍሳዊ ድኀነትን የማያካትት በመሆኑ ነው።

ክህነት በብሉይ ኪዳን፤  ከአሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆች በነገደ ሌዊ የተላለፈ ሲሆን የቤተሰብ መሆኑ ቀርቶ የነገድ ክህነት መሆኑን እናያለን። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስረዳን ይህ ሥርዓት የተጀመረው በእግዚአብሔር ወዳጅ በሙሴ አማካይነት ሲሆን ሙሴ ቀጥታ ከእግዚአብሔር በመነጋገር የመሠረተው ስለሆነ ሕጉ፣ሥርዓቱ ከእግዚአብሔር የተሰጠ እንጂ ሰው ሠራሽ ባለመሆኑ እስከ ሐዲስ ኪዳን ዘመን ድረስ አገልግሎአል። ካህናቱም ከመሥዋዕት፣ጸሎት፣ ተግሣጽና ምክር በተጨማሪ ትንቢት የመናገር ሀብት ያላቸውም ነበሩ። ከእነዚህም ነገሥታት፣ ነብያት፣ መሣፍንት ይገኙበታል። በዚህ ዘመን ውስጥ ግን ክህነቱ ተሰጥቶአቸው ድርሻቸውን በአግባቡ የተወጡ ብዙዎች ሲሆኑ ባለመወጣታቸው እና ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን ክህነት ባለመጠበቃቸው የተቀጡም አሉ። ለምሳሌ የኤሊ ልጆች አፍኔ እና ፊንሐስ እራሳቸው እነደጠፉ ታቦተ ሕጉንም እንዳስማረኩ ህዝቡንም እንዳጠፉና እንዳዋረዱ እናያለን። ክህነት ሳይፈቀድላቸው በጉልበት፣ በትምክሕት ተነሳሥተው ለማገልገል ሞክረው የጠፉም አሉ። በሙሴና በአሮን ዘመን የነበሩ ዳታን አቤሮን ሌሎችም ይጠቀሳሉ።

ክህነት በሐዲስ ኪዳን፤ ደግሞ የተመሠረተው በራሱ በባለቤቱ በጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። “ለሊሁ ሠዋዒ ወለሊሁ ተሠዋዒ” ቅዱስ ጳውሎስ በዕብራውያን ምልእክቱ እንዳስተማረን እራሱ መሥዋዕት እራሱ ካህን (የመሥዋዕቱ አቅራቢ) ሆኖ ነው ያዳነን። ዕብ ፲፣፲፪ ይህም ክህነት የእርሱ የባህርይው ሲሆን ለቅዱሳን ሐዋርያት ደግሞ ጸጋውን በመሥጠት ከእነርሱ ቀጥሎ በእነርሱ ለሚተካ አምኖ፣ ተጠምቆ፣ ተምሮ እንዲሁም ሕጉን፣ ትዕዛዙን፣ ሥርዓቱን ጠብቆ ለተገኘ ሁሉ ትምህርቱ፣ እምነቱና ትህትናው እየታየ ዘር፣ቀለም፣ቋንቋ፣ነገድ፣ ሥልጣን ፣ሀብት፣ ቦታ ሳይለይ ሁሉም መሾም እንደሚችሉ ሥልጣን ሰጠ። ይህ ሥልጣን እስከ ዓለም ፍጻሜ የማሠር፣የመፍታት፣ መንግሥተ ሰማያትን የመዝጋትና የመክፈት ሥልጣን፣ ይቅር ላላችሁዋቸው ይቅር እላቸዋለሁ፤ይቅር ላላላችሁአቸው ግን ይቅር አልላቸውም የተባለልን ቅዱስ ጴጥሮስን ትወደኛለህ ብሎ ሦስት ጊዜ በመጠየቅ በጎቼን ጠብቅ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ፣ ግልገሎቼን ጠብቅ ያለበት የመጠበቅ የማሠርና የመፍታት፣ ይቅር የማለት ሥልጣን ነው። መናዘዝ ማለት በኃጢያቱ ተጸጽቶ ከእግዚአብሔር ይቅርታን ለማግኘት ወደ ካህን የቀረበን ተነሳሂ፤ ንሥሐን ሰጥቶ በንሥሐ ሥርየት ወደ አምላክ ማቅረብ ማለት ነው።

ይህ ክህነት ለህዝብ፣ ለአህዛብ ሁሉ፣ እንዲሁም ለአመነ፣ ለተጠመቀና ለተማረ ሥለተፈቀደ፡ ክህነተ ብዙኃን ይባላል። አሰጣጡ ግን ሕግና ሥርዓት አለው። ከቅዱሳን ሐዋርያት ተያይዞ የመጣ በመሆኑ የነሱ ተተኪዎች በሆኑት በብጹአን ሊቃነ ጳጳሳት ካልሆነ በቀር በሌላ አይሠጥም ወይንም አይሰየምም።

ይቆየን!

ርእሰ ደብር ብርሃኑ አካል

ጥቅምት ፳፯ ተዝካረ ስቅለቱ ለእግዚእነ

በኩረ ፍሥሐ ቀሲስ ኃይለኢየሱስ ተመስገን

ጥቅምት ፳፯ ተዝካረ ስቅለቱ ለእግዚእነ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

እንኳን ለመድኃኔዓለም ዓመታዊ ክብረ በዓል ዝክረ ጥንተ ስቅለት አደረሳችሁ አደረሰን

ከሁሉ አስቀድሞ ሃይማኖትን መመስከር እንዲገባ “ ከመዝ ነአምን ዘአልቦቱ እም በሰማያት፤ ወአብ በዲበ ምድር ” በሰማይ ያለእናት ከአብ መወለዱን፣ በምድርም ያለ አባት ከድንግል ማርያም መወለዱን እናምናለን። ይህንንም አባቶቻችን ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ቅድመ ዓለም ከእግዚአብሔር አብ ያለ እናት፣ አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ የተወለደ ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው አካላዊ ቃል ፤ ድኀረ ዓለም ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ያለ አባት፣ መለወጥ ሳያገኛት ዘር ምክንያት ሳይሆን ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ የተወለደ፤ ወልደ እግዚአብሔር በመለኮቱ ወልደ ማርያም በትስብእቱ ብለው አምልተው እንዲያስተምሩን  “ከመ አሐዱ ውእቱ ባሕቲቱ ውእቱ አምላክ ወሰብእ ኅቡረ” ትርጉሙም  እርሱ በተዋሕዶ ሰው የሆነ አምላክ ነው ማለት ነው።  ሃይማኖተ አበው ዘጎርጎርዮስ ፴፭፥፳፩

 

መጋቢት ፳፯  በቃል መነገሩ በልብ መታሰቡ ከፍ ከፍ ይበልና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  የተሠቀለበት ጥንተ ስቅለቱ የሚታሰብበት ቀን ነው ፡፡  ይሁን እንጂ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን በዲሜጥሮስ ቀመር መሠረት አጽዋማትን በጠበቀ መልኩ ከትንሣኤ በዓል በፊት ያለውን አርብ “ስቅለት” ተብሎ እንዲከበር ሥርአት ሠርተዋል፡፡መጋቢት ፳፯ ቀን በዓቢይ ጾም ስለሚውል በዓቢይ ጾም ሀዘን እንጂ ደስታ ስለሌለ በዓል ማክበርም ስለማይፈቀድ፤ ወደ ጥቅምት ፳፯ ተዛውሮ ደስ ብሎን እንድናከብረው ቤተክርስቲያን ሥርዓት ሰርታለች ።

 

ጥቅምት ፳፯ ዝክረ ጥንተ ስቅለቱን ቤተክርስቲያናችን ጌታችን በመስቀሉ ስለፈጸመልን የማዳን ስራ “ በመስቀሉ ወበቃሉ አዕበዮሙ ለአበዊነ ” ። በመስቀሉና በቃሉ አባቶቻችንን ከፍ ከፍ አደረጋቸው እያለች እየዘመረች ታስበዋለች። ከዚህም በተጨማሪ ጥቅምት ፳፯  በወርኀ ጽጌ ውስጥ ያለ በመሆኑ “  …እስመ ውእቱ ክብሮሙ ለቅዱሳን መድኃኒቶሙ ለጻድቃን  አሠርገዋ ለምድር በጽጌ ሮማን ስብሐተ ዋህድ ዘምስለ ምህረት በመስቀሉ ወበቃሉ አዕበዮሙ ለአበዊነ ” እያለች የቅዱሳን ክብራቸው የጻድቃን መድኃኒት የሆነው ጌታ ምድርን በአበባ የሚያስጌጣት እንደሆነ በመመስከር ትዘምራለች ።

“እስመ አንተ ትክል አንጽሖትየ እግዚኦ  ወበቃልከ እለ ለምፅ አንጻሕከ  ወበጽጌያት ምድረ አሠርጐከ  ወበመስቀልከ ለጻድቃን አብራህከ ”  ልታነጻኝ ይቻልሃል አቤቱ ለምጻሞቹን በቃልህ እንጽተሃልና እያሉ አባቶቻችን በመስቀሉ ለጻድቃን ማብራቱን እያሰቡ በዓሉን በመዝሙር በደስታ ያከብሩታል

 

ወበከመ ሙሴ ሰቀሎ ለአርዌ ምድር በገዳም ከማሁ ሀለዎ ለወልደ ዕጓለ እመሕያው ይሰቀል” ዮሐ ፫፥፲፬ ሙሴ እባብ በምድረ በዳ እንደሰቀለ የሰው ልጅ ክርስቶስ ይሰቀል ዘንድ አለው  ብሎ እንደተናገረ  የክብር ባለቤት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ዓለም ድኅነት የተሰቀለው መጋቢት ፳፯ ቀን ነው ።

 

ክርስቶስ ስለስቅለቱ ሲናገር ምሳሌ የሚሆነውን፣ ሙሴ በምድረ ባዳ የሰቀለውን፣ የነሐሱን እባብ “ሙሴ እባብ በምድረ በዳ እንደሰቀለ የሰው ልጅ ክርስቶስ ይሰቀል ዘንድ አለው” ብሎ ምሳሌውን ተናግሯል።

 

የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እስራኤልን ከደመና መና አውርዶ፣ከጭንጫ ውሀ አፍልቆ ቢመግባቸው ከዚህ ምድሩ ብቅ፣ሰማዩ ዝቅ ቢልለት፣ ከደጋ ላይ ቢሆንለት የውርጭ ሰደቃ እያበጀ፣ ውሀውን እያረጋ፣ መና መገብኳችሁ ይላል እንጅ ይክልኑ እግዚአብሔር ሠሪዓ ማዕድ በገዳም። ቆላ በሆነማ ባልተቻለውም ነበር ብለዋል ።ጌታም ሊያስተምራቸው ፣  የርሱን ከሃሊነት ሊያሳያቸው፣  የእነርሱንም ሀሰት ሊገልጥባቸው ፣  ሙሴን ነቅዓ ማይ የሌለበት በርሐ ይዘሀቸው ውረድ ብሎት ቢሄዱ መናው ወርዶላቸዋል፣ ውሀውም ፈልቆላቸዋል ።ነገር ግን ነዘር የሚባል እባብ እየነከሰ ይፈጃቸው ጀመር።ከዚህ በኋላ እስራኤል ሙሴ ዘንድ ሂደው ከጌታ ምህረት ቸርነት ከሰው ስሕተት ኃጢአት አይታጣም በእግዚአብሔርና በአንተ ላይ ተናግረን በድለናል  እባቦችን ከኛ ያርቅልን ዘንድ ወደ እግዚአብሔር አመልክትልን አማልደን አሉት።ሙሴም ስለሕዝቡ  ወደ እግዚአብሔር ቢጸልይ  ጽሩዩን ብርት አርዌ አስመስለህ ሠርተህ ከሚገናኙበት አደባባይ ከእንጨት ላይ ስቀልላቸው አለው። ሙሴም እባብን ሠርቶ በዓላማ ላይ ሰቀለ እባብም የነደፈችው ሰው ሁሉ የነሐሱን እባብ ባየ ጊዜ ዳነ። (ኦሪ ዘኁ ፳፩ ፥፩፡፱)

 

ይህንም ምሳሌ አባቶቻችን በትርጓሜ ወንጌል ቅዱስ እንዳስቀመጡልን አርዌ ምድር የዲያብሎስ፤አርዌ ብርት የጌታ ምሳሌ ነው ። በአርዌ ምድር(እባብ) መርዝ እንዳለበት በዲያብሎስም ፍዳ ኃጢአት አለበት።በአርዌ ብርት መርዝ እንደሌለበት በጌታም ፍዳ ኃጢአት የለበትም ።አርዌ ብርት በአርዌ ምድር አምሳል መሰቀሉ ጌታ በአምሳለ እኩያን እንደወንጀለኛ ተቆጥሮ ለመሰቀሉ ምሳሌ ነው። ዳግመኛም  “ተኈለቈ ምስለ ጊጉያን” ከዐመፀኞችም ጋር ተቈጥሯልና  ኢሳ  ፶፫፥፲፪  የሚለውን ትንቢት ፈጽሟል። ምሳሌውን አውቆ አስመስሏል ትንቢቱንም አውቆ አናግሯል ።

 

ጲላጦስ አይሁድን ከሁለቱ ማናቸውን ላድንላችሁ ትወዳላችሁ ቢላቸው በርባንን ፍታልን ክርስቶስ የተባለ ኢየሱስን ግን ስቀለው አሉ ።ጲላጦስም  በዚህ ሰው ደም ከመጣ ፍዳ ሁሉ ንጹሕ ነኝ ብሎ ባደባባይ እጁን ታጠበ። አይሁድ ደሙ በኛም በልጅ ልጆቻችንም ይሁን አሉ። እርሱም በርባንን ፈታላቸው ጌታንም አሳልፎ ሰጣቸው። ማቴ ፳፯ ፥፳፭

 

ቅዳሴ ዮሐንስ አፈወርቅ “ሊቃነ መላእክት በመፍራትና በመንቀጥቀጥ ከፊቱ የሚቆሙለትን በአደባባይ አቆሙት፤ ኃጢያትን ይቅር የሚለውን ኃጥእ አሉት፤ በመኳንንት በሚፈርደው በርሱ ፈረዱበት” ፡፡  እንዲል ክርስቶስን አይሁድ ስቀለው ብለው ፈረዱበት

 

አክሊልን የሚያቀናጀውን የነገሥታት ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስን አነገስንህ ብለውታልና ጭፍሮች በፍና ተሣልቆ የእሾህ አክሊል ታተው ደፉለት “ወጸፈሩ ሐራ አክሊለ ዘሦክ ወአስተቀጸልዎ ዲበ ርእሱ” ዮሐ ፲፱፥፪ ። ኢየሱስ ክርስቶስ  የእሾኽ አክሊል በመቀዳጀቱ ዕፀ በለስን በልቶ  “ምድር እሾኽንና አሜከላን ታበቅልብኻለች” ዘፍ  ፫፥፲፰  ብሎ የፈረደበትን አዳም  ስለርሱ ክሶ መርገሙን ደምስሶለታል ።

 

መጋቢት ፳፯ ቀን ክርስቶስ ኢየሱስ በመስቀል በተሰቀለ ጊዜ፤ የተሰቀለው የክብር ባለቤት ሰማይን የፈጠረ ነውና  ፀሐይ ጨልማለች፣ ጨረቃ ደም ሆኗል፣ ከዋክብት ረግፈዋል። የተሰቀለው የክብር ባለቤት ምድርንም የፈጠረ ነውና በምድር የቤተ መቅደሱ መጋረጃ ከላይ እስከ ታች ለኹለት ተቀዷል፤ ምድር ተናውጣ ዐለቶች ተሠንጥቀዋል፤ መቃብራት ተከፍተዋል፤ ከ፭፻ በላይ ሙታን ተነሥተዋል (ማቴ ፳፯ )፡፡

 

ኦ አእዳው እለ ለሐኳሁ ለአዳም ተቀነዋ በቅንዋተ መስቀል ፤ ኦ አእጋር እለ አንሶሰዋ ውስተ ገነት ተቀነዋ በቅንዋተ መስቀል

አዳምን የፈጠሩ እጆች በመስቀል ቀኖት ተቸነከሩ ወዮ፤በገነት የተመላለሱ እግሮች በመስቀል ቀኖት ተቸነከሩ ወዮ፡፡ እንዲል  ቅዳሴ ዮሐንስ አፈወርቅ ስቅለቱን በዲሜጥሮስ ቀመር አውጥተን የጌታን መከራውን አስበን በስግደት ህማማቱን እናስባለን በዝክረ ጥንተ ስቅለቱ በጥቅምት ፳፯ ደግሞ በመስቀል የተደረገልንን አስበን እናመሰግነዋለን፡፡

 

ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የስቅለት መታሰቢያ ጋር  ቤተ ክርስቲያን በ15ኛው መ.ክ.ዘ  የነበሩትን አቡነ መብዓ ጽዮንን ታስባለች፡፡  አቡነ መብዓ ጽዮንን  አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን  ‹‹ በዕለተ ዓርብ የተቀበልከውን  መከራ ግለጽልኝ ››ብለው በጸለዩ ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ የተቀበላቸውን መከራዎች ሁሉ አሳያቸው፡፡ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ከርስቶስን መከራ ካዩበት ቀን ጀምሮ ሕማሙን መከራውን ግርፋቱን እስራቱንበጠቅላላ አስራ ሦስቱን ሕማማተ መስቀል በማሰብ ጀርባቸውን በአለንጋ ይገርፉ ፤ ራሳቸውን በዘንግ ይመቱ ነበር፡፡  የጌታችንን ሕማማተ መስቀል እያሰቡ ዘወትር ስለሚያለቅሱ  ዐይናቸው ጠፍቶ ነበር፡፡ ነገር ግን እመቤታችንቅድስት ድንግል ማርያም  የብርሃን ጽዋ ይዛ መጥታ ዐይናቸውን ቀብታ አድናቸዋለች፡፡ በዚህ የተነሳ ‹‹በትረ ማርያም›› እየተባሉ እንደሚጠሩ ገድላቸው ያስረዳል፡፡ በዚህ መሰረት ጥቅምት ፳፯ ቀን ለአቡነ መብዓ ጽዮን ቃልኪዳን የገባበት ቀን በመሆኑ በየዓመቱ ጥቅምት ፳፯  ቀን ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ዝክረ ጥንተ  ስቅለቱ ጋር ይከበራል፡፡ የጻድቁ አቡነ መብዓ ጽዮን በረከትና ረድኤት ይደርብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

በኒውዮርክና ኒውጀርሲ የሚገኙ አብያተ ክርስትያናት የአንድነት ጉባኤ አካሄዱ

በኒውዮርክና ኒውጀርሲ የሚገኙ አብያተ ክርስትያናት የአንድነት ጉባኤ አካሄዱ

ታላላቅ ሊቃውንተ ቤተ ክርስትያን ፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ምዕመናን በተገኙበት በደመቀ ሁኔታ የሰላም እና የአንድነት ጉባኤ በሰሜን አሜሪካ ኒዋርክ ኒውጀርሲ ብስራተ ገብርኤል ቤተ ክርስትያን ጥቅምት ፫ ፳፻፲፩ ዓ.ም ተካሄደ። የኒውዮርክ ጽዮን ቅድስት ማርያም አስተዳዳሪ መልአከ ገነት ገዛኸኝ ፀሎተ ቅዳሴውን የመሩት ሲሆን ፣ የዕለቱ ትምህርተ ወንጌል “ምሕረትን እወዳለሁ’’ (ማቴ ፱፡፲፫) በሚል ርዕስ በመጋቤ ወንጌል ኤልያስ የብስራተ ገብርኤል ቤተ ክርስትያን ሰባኬ ወንጌል ተሰጥተዋል። በመቀጠል መልአከ ሰላም ዳኛቸው በእንግሊዝኛ ትምህርት የሰጡ ሲሆን ያለፈውን የመለያየት ዘመን ለቤተ ክርስትያን የጨለማ ጊዜ እንደነበረ አስታዉሰው ከዚህ በኋላ ግን ቤተ ክርስትያንን በአንድነት ማገልገል እንደሚገባ መልእክት አስተላልፈዋል። በዚህ ጉባኤ በ ኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ከሁለት የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተናጋሪ አብያተ ክርስትያናት የመጡ ምዕመናን ተገኝተዋል።በዓሉን በተመለከተ ከሁሉም አብያተ ክርስትያናት የተውጣጡ ህፃናት እና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች መዝሙር አቅርበዋል።

በመቀጠል የኒውዮርክ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስትያን አገልጋይ ርዕሰ መምህራን ብርሃኑ በዓሉን በተመለከተ የቅዱስ ያሬድ ወረቦችን አሰምተዋል። ምዕመናን በዕልልታ እና በጭብጨባ ከሊቃውንቱ እና ከመዘምራን ጋር አብሮ በመዘመር ለዚህ አንድነት ያበቃቸውን እግዚአብሔርን አመስግነዋል። ቅዳሴው፥ዝማሬው ልብን የሚመሰጥ ፣ መንፈስን የሚያድስ እና የሚያረጋጋ እጅግ በጣም ልዩ ነበር። ቀጥሎም የደስታ መግለጫ መልአከ ገነት ገዛኸኝ ያቀረቡ ሲሆን መለያየት ጥሩ ባይሆንም ቤተ ክርስትያን እንድትሰፋ ምክንያት ሁኗል ብለዋል። ከዚህ በኋላ ግን ቤተ ክርስትያንን በአንድነት በማገልገል እንደ መስቀል እና ጥምቀት ያሉ ዓበይት በዓላትን በጋራ ማክበር እንደሚገባ መክረዋል።ርዕሰ መምህራን ብርሃኑ ተመሳሳይ መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን መወድስ ቅኔ በግዕዝ እና በአማርኛ ቀርቧል። በተለይ የሴራክዮስ ገነተ ደናግል ቅድስት አርሴማ ወክርስቶስ ሠምራ ገዳም አስተዳዳሪ የሆኑት መልአከ ገነት ካሳሁን እንባ እየተናነቃቸው ያስተላለፉት መልእክት የብዙዎችን ልብ የነካ ነበር። ቤተ ክርስትያን  የማሕበረሰብ (Community) አገልግሎት ሳይሆን ምዕመናንን ቅዱስ ስጋውን ክቡር ደሙን ተቀብለው ወደ መንግስተ ሰማያት ለመግባት የሚዘጋጁባት ቤተ መቅደስ መሆን እንዳለባት እና በተለይም ተተኪ ትውልድ ላይ በእጅጉ መስራት እንደሚገባ ገልፀዋል። በመጨረሻም ሰርሆተ ሕዝብ ከሆነ በኋላ በብስራተ ገብርኤል ቤተ ክርስትያን አዳራሽ ጉባኤው ቀጥሎ ውሏል።

ምዕመናን አስቀድመው ቦታቸውን የያዙ ሲሆን አባቶች ካህናት ሲገቡ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች በመዝሙር ፣ በዕልልታ እና በጭብጨባ በመቀበል ለአባቶች ካህናት ያላቸውን አክብሮት ገልፀዋል።በተጨማሪ ዲያቆን ዘካርያስ እና ዘማሪ መንግስቱ ወቅቱን የተመለከቱ መዝሙራትን በማቅረብ በዓሉን አድምቀውታል።  በዚሁ ጉባኤ በUN የኢትዮጵያ አምባሳደር ታዬ አጽቀ ስላሴ ተገኝተዋል። የአዘጋጅ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ወንድም አገኘሁ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት አስተላልፈዋል። አክለውም ይህንን የአባቶች አንድነት እንዲመጣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ላደረጉት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አመስግነዋል። በመቀጠል ንግግር ያደረጉት አምባሳደር ታዬ አጽቀ ስላሴ ሲሆኑ የምስጋና መልዕክቱ በአግባቡና በስርዓቱ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ እንደሚያስተላልፉ ቃል ገብተዋል። በተጨማሪም ቤተ ክርስትያን ለአገር አንድነትና ሰላም ያደረገችው አስተዋፅኦ ከፍተኛ መሆኑን ገልፀዋል። በመቀጠል የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች የደብረ ገነት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስትያን ተወካይ ወጣት መኮንን ቤተ ክርስትያን አፍሪካን አሜሪካን (African American) በእንግሊዝኛ ቋንቋ በማስተማር እንድትደርስላቸው ተማፅነዋል። ከዚህ በኋላ የእንግሊዝኛ ተናጋሪዎች የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች መዝሙር በእንግሊዝኛ፤በግዕዝ፤በአማርኛ አቅርበዋል።

በተጨማሪ የኒውዮርክ ደብረ ብርሃን ቅድስት ስላሴ (በሰሜን አሜሪካ የመጀመርያው የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ) አስተዳዳሪ መጋቤ አእላፍ ኤፍሬም የደስታ መግለጫ መልእክት አስተላልፈዋል። በተመሳሳይ መልኩ ሌሎች የቤተ ክርስትያን አስተዳዳሪ አባቶች ካህናት የተሰማቸውን የደስታ መግለጫ  መልእክት አቅርበዋል።ቀጥሎም በሰሜን አሜሪካ የማህበረ ቅዱሳን የኒውዮርክ ግንኙነት ጣብያ ሰብሳቢ ዲያቆን ዶክተር ምሕረተአብ “ዕርቅ የሚያደርጉ ብፁዓን ናቸው፤ እነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና“ (ማቴ ፭፥፱) በሚል መነሻ ርዕስ ማህበሩ በአባቶች አንድነት የተሰማውን ደስታ ገልፀዋል። የማህበሩ አባላትም ልጆችን በማስተማር እና መዝሙራትን በማቕረብ ተሳትፈዋል። በመጨረሻም የአዘጋጅ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ወንድም አገኘሁ ይህንን ጉባኤ ያዘጋጁ ከ ፲፩ አብያተ ክርስትያናት የተውጣጡና ከማህበረ ቅዱሳን የተወከሉ ፪ አባላት በድምሩ ፳፬ አባላት እና በአጠቃላይ ይህንን ጉባኤ እንዲሳካ ለደከሙት ሁሉ ምስጋና በማቅረብ በአባቶች ካህናት ጸሎትና ቡራኬ የጉባኤው ፍጻሜ ሁኗል።