ከትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ ያሉት ዕለታት ስያሜያቸውና ታሪካዊ አመጣጣቸው

ዲያቆን ተመስገን ዘገየ

ከትንሣኤ ሌሊት ፩ ሰዓት ጀምሮ እስከ ዳግም ትንሣኤ ያለው ሳምንት የፉሲካ ምሥጢር የተገለጠበት፤ ከግብፅ ወደ ምድረርስት ከሲኦል ወደ ገነት መሻገርን የሚያመላክት ሳምንት ነው። ለፉሲካ የሚታረደውም በግ ፉሲካ ይባላል (ዘዳ. ፲፮÷፪:፭÷፮)፤ ፉሲካ ማለት ደግሞ ማለፍ ነው፤ ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበትም ሳምንት የፉሲካ ሳምንት ነበር፤ (ሉቃ. ፳፪፥፲፬-፲፮፤ ዮሐ. ፲፰፥፴፰-፵)።

እርሱም ንጹሕ የእግዚአብሔር በግ ሆኖ ደሙን ስላፈሰሰልን ፉሲካችን ክርስቶስ ተባለ፤ ብሉይ ደግሞ የሐዲስ አምሳል ነው። ይኸውም ሙሴ የእስራኤልን ሕዝብ ባሕረ ኤርትራን ካሻገራቸው በኋላ ወደ ምድረ ርስት፤ ነፍሳት ደግሞ በክርስቶስ መሪነት ከሲኦል ወደ ገነት መግባታቸውን የሚገልጽ ነው፡፡ ዕለቱም ሙሴ የወልደ እግዚአብሔር፤ በትረ ሙሴ የመስቀል ምሳሌ፤ግብፅ የሲኦል፤ የገሃነመ እሳት፤ የፈርዖን የዲያብሎስ፤ ሠራዊቱ የሠራዊተ ዲያብሎስ፤ እስራኤል የምእመናንና ባሕረ ኤርትራ የባሕረ ሲኦል ምሳሌ ነው፡፡

ሰኞ– ማዕዶት (ፀአተ ሲኦል)

ማዕዶት የቃሉ ትርጓሜ መሻገር ሲሆን፤ በዚህ ቀን ቤተ ክርስቲያን ነፍሳት በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከሐሳር ወደ ክብር፤ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሲኦል ወደ ገነት መሻገራቸውንና ፉሲካችን ክርስቶስ መሆኑን ታስባለች።

ማክሰኞ– ቶማስ

ቅዱስ ቶማስ በጦር የተወጋ ጎኑን፤ በቀኖት የተቸነከረው እጁንና እግሩን ካላየሁ አላምንም በማለቱ ክርስቶስም «ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤እጅህንም አምጣና ወደ ጎኔ አግባ፤ እመን እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን» ብሎታል። ቶማስም «ጌታዬ አምላኬም»፤ ብሎ በመለሰ ጊዜ ጌታችን ኢየሱስም «ስለ አየኸኝ አመንህን? ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዓንስ ናቸው» አለው (ዮሐ ፳፥፳፯-፳፱)፤ ቶማስ የጌታን ፍቅር ተገንዝቦ ትንሣኤውን ስላመነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዕለቱን ቶማስ ብላ ታስበዋለች።

ዲዲሞስ የተባለ ከአሥራ አንዱ ደቀ መዛሙር አንዱ ቶማስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዝግ ቤት ገብቶ «ሰላም ለሁላችሁ ይሁን» ባላቸው ጊዜ ከእርሳቸው ጋራ አልነበረም»። ከ፲፪ቱ ሐዋርያት አንዱ (ማቴ. ፲፥፪-፫) ቶማስ በአራማይክ ዲዲሞስ በግሪክ መንታ ማለት ነው፤ (ዮሐ. ፳፥፳፬)፡፡ ቶማስ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ በፋርስና በሕንድ ወንጌልን እንዳስተማረ ይነገራል። ለቶማስ ጎኑን እንዲዳስስ የፈቀደው ለሌሎችም ቅዱሳን ሐዋርያት የተቸነከረውን እጅና እግሩን ያሳየው ካህናት ሥጋውና ደሙን እንዲፈትቱ ነው፤ ዮሐንስም በእጃችን ዳሰስነው ብሏል፤ (ሉቃ. ፳፬፥፴፱)፡፡

ለማርያም መግደላዊት ግን የተነሣ ዕለት አትንኪኝ ማለቱ ለሴቶች ሥጋውን ደሙን መፈተት አልተፈቀደም ሲል ነው ብለው ሊቃውንት ያትታሉ፤ «አትንኪኝ፤ ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና፤ ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሂጅና፡- ወደ አባቴ÷ ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬ÷ ወደ አምላካችሁም አርጋለሁ አለ ብለሽ ንገሪአቸው» አላት፤ (ዮሐ. ፳፥፲፯)። ገቦ መለኮቱን የዳሰሰች እጁ በሕይወት ትኖራለች፤ በሕንድ ሀገር ከታቦት ጋር በመንበር ላይ ትኖራለች። በየዓመቱ በእመቤታችን በዓል በአስተርእዮ ሊያጥኑ ሲገቡ የሚሾመውን ወጥታ ቀኝ እጁን ትይዘዋለች፤ ዓመት አገልግሎ ያርፋል።

ረቡዕ –አልዓዛር

አልዓዛር ክርስቶስ ያስነሣው የማርያምና የማርታ ወንድም ነው፤ የስሙም ትርጓሜ እግዚአብሔር ረድቷል ማለት ነው፤ (ዮሐ. ፲፩፥፯-፵፰)፤ አልዓዛር የሞተው መጋቢት ፲፯ ነበር፡፡ እህቶቹም ክርስቶስ እንዲመጣ መልእክት ልከውበት ነበር፤ ክርስቶስ ግን በ፬ኛው ቀን ማለትም መጋቢት ፳ መጥቶ ከሞት አስነሥቶታል፤(ዮሐ.፲፩፥፵፬)፡፡ ፋሲካውንም በወዳጁ በአልዓዛር ቤት ያከብር ዘንድ ከቀደ መዛሙርቱ ጴጥሮስንና ዮሐንስን አስቀድሞ ላከ፤ ከዚያም በአልዓዛር ቤት ሆኖ የሐዲስ ኪዳንን ሥርዓት ምሥጢረ ቁርባንን ሰርቶ ለደቀ መዛሙርቱ አሳያቸው፤ አልዓዛር ከተነሣ በኋላ በሐዋርያት ኤጲስ ቆጶስነት ተሸሞ ፵ ዓመት አገልግሎ ግንቦት ፳፯ ቀን ዐርፏል (ስንክሳር ግንቦት ፳፯)፡፡

አዳም ሐሙስ

አዳም የመጀመሪያ ሰውና የሰው ሁሉ አባት ነው፤ በ፮ኛው ቀን የተፈጠረ የሰው ሁሉ ምንጭ ስለሆነ የሰው ዘር ሁሉ ከእርሱ ተገኝቷል፡፡ በዚህ ዕለት ለአዳም የተሰጠው የተስፋ ቃል ስለመፈጸሙ፤ (ዘፍ. ፫÷፲፭) አዳም ከነልጆቹ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻ ስለመውጣቱ ይታሰብበታል፡፡ ክርስቶስ በተነሳበት በአምስተኛው ቀን ሐሙስ አዳም ይባላል፤ ጌታችን አዳምን ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ብሎ ቃል ገብቶለት እንደነበር በቀሌምንጦስ ተጽፏል፡፡

አዳምና ሔዋን በገነት ፯ ዓመት ከቆዩ በኋላ ትእዛዙን በመተላለፋቸው ከኤደን ገነት አስወጣቸው (ኩፋ.፬፥፲፮፤ዘፍ.፫፥፳፫) «ብዙ ተባዙ» ያለው ቃል እንዳይቀር በምድር ላይ ወርደው ልጆችን ወለዱ ይላል፡፡ የተወለዱትም ልጆችም በቁጥር ፷ እንደሆኑ (፩መቃ. ፳፰፥፮) የተወለዱት ልጆች ደጎችና ክፉዎች እንደ ነበሩ በአቤልና በቃየል ታውቋል፤ (ዘፍ. ፬፥፰)፤ አዳም በዚህ ዓለም ፱፻፴ ዓመት ኑሮ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በ፵፻፭፻፸ ሚያዚያ ፮ ዐርፏል፡፡

ዐርብ– ቤተ ክርስቲያን

ዐርብ የእግዚአብሔር ቅድስት ማደሪያ በሆነችው ቤተ ክርስቲያን ተሰይማለች፤ ይህም ሁሉም ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን የተፈጸመባት ዕለት በመሆኗ ነው፤ ዕለተ ዐርብ፤ የሥራ መከተቻ፤ ምዕራብና መግቢያ በሚሉት ስያሜዎችም ትጠራለች፡፡

በዕለቱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል ያደረገውን ተአምር በመስቀሉ ድኅነትን እንዳሳየ፤ በቀራንዮ የሕንጻዋ መሠረት እንደተተከለላትና ሥጋ መለኮት እንደተቆረሰላት፤ ልጆቿን ከማሕፀነ ዮርዳኖስና ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ የምትወልድበት ማየ ገቦ እንደፈሰሰላት ተገልጾባታል፤(ኤፍ.፪፥፲፱፤ራዕ.፩፥፮-፰)፡፡

ቅዳሜ– ቅዱሳት አንስት

ቅዳሜ ቅዱሳት አንስት ተብሎ ይጠራል፤ ይህም ስያሜ በስቅለት ዕለት በልቅሶና በዋይታ የሸኙትን፤(ሉቃ. ፳፫፥፳፯) በዕለተ ትንሣኤ ሽቱና አበባ ይዘው ወደ መቃብር የገሰገሱትን፤ ከሁሉም ቀድሞ ጌታችን በዕለተ ሰንበት ተነሥቶ ለተገለጸላቸው ማርያም መግደላዊት፤ የታናሹ ያዕቆብ እና የዮሳ እናት ማርያም፤ የዘብዴዎስም የልጆቹ እናት ሰሎሜንም መታሰቢያ ለማድረግ ነው፤«ከሳንምንቱ በመጀመሪያዩቱ ቀን ያዘጋጁትን ሽቶ ይዘው እጅግ ማልደው ወደ መቃብሩ ሄዱ፤ሌሎች ሴቶችም አብረዋቸው ነበሩ (ሉቃ. ፳፬ ፥ ፩ )፡፡

እሑድ– ዳግም ትንሣኤ

«ያም ከሳምንቱ የመጀመሪያው ቀን በመሸ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ አይሁድን ስለ ፈሩ ተሰብስበው የነበሩት ቤት ደጁ ተቆልፎ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ መጥቶ በመካከላቸው ቆመና÷«ሰላም ለእናንተ ይሁን» አላቸው፤ ማቴ.፳፥፲፱፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከደቀ መዛሙርቱ ተሰውሮ ከሰነበተ በኋላ በዕለተ እሑድ በዝግ ቤት እንዳሉ ዳግም ተገለጸላቸው፤ስለዚህም ዳግም ትንሣኤ ተባለ፡፡

(ምንጭ:-መዝሙረ ማኅሌት ወቅዳሴ፤ ሥርዓተ አምልኮ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ፤ የዮሐንስ ወንጌል አንድምታ፤ ምዕ. ፳፥፳፬)

በዓለ ግዝረት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

በዓለ ግዝረት

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅድመ ዓለም በህሊና ያሰበውን፤ ድኅረ ዓለም በነቢያት ያናገረውን ለመፈጸም ሰው ሆነ፣ ሥጋ ለበሰ፤ ሕግ ጠባያዊን ሕግ መጽሐፋዊን እየፈጸመ በጥቂቱ አደገ። ሕግ ጠባያዊ፤ አበ፣ እመ ማለት፣ ለዘመድ መታዘዝ፣ በየጥቂቱ ማደግ ነው። “ወልህቀ በበኅቅ እንዘይትኤዘዝ ለአዝማዲሁ ወለይእቲ እሙ” እንዲል። ሕግ መጽሐፋዊ በስምንት ቀን ቤተ ግዝረት በአርባ ቀን ዕጉለ ርግብ ዘውገ ማዕነቅ ይዞ ቤተ መቅደስ መግባት የመሳሰሉት ናቸው፤ በማለት የመጻሕፍተ ሐዲስ ኪዳን ሊቃውንት በሐዲስ ኪዳን ትርጓሜ መግቢያ ላይ ያመሰጥራሉ፣ ያስተምራሉ።

ቅዱስ ሉቃስ በጻፈው የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ወንጌል ምዕራፍ 1 ቁጥር 59 ላይ ዘግቦልን እንደምናገኘው፤ በዘመነ ብሉይ ወንድ ልጅ በተወለደ በስምንተኛው ቀን ሲገረዝ ስም ይወጣለት ነበር።በመሆኑም ግዝረት የሥጋ ሸለፈት መቆረጥን ያመለክታል።

የግዝረት ሥርዓት ዝም ብሎ የመጣ ሳይሆን እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠው የቃል ኪዳኑ ምልክት ነው። ዘፍ17 ፤ 7-14 በሙሴ የመሪነት ዘመንም ለእስራኤል ህዝብ ምልክትና መለያ ነበር።ዘፀ 12፤43 ፈሪሳውያን ግን ከአብርሃም የመጣ መሆኑን ሳይረዱ በሙሴ እንደተሰጠ ሕጋዊና ሕዝባዊ ምልክት አድርገው ያምኑ ነበር።የሐዋ 15፤1-5 ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን፤ መጀመሪያ ራሱ የሰጠው ለአብርሃም እንደነበርና መንፈሳዊ ምልክትም እንደሆነ አስረድቷቸው ነበር።ዮኀ 7፤22።

የሚከተሉት ሦስት ነጥቦች የግዝረት ዋና ዋና ዓላማዎች ናቸው።

  1. እግዚአብሔር የተገረዘውን ሰው ለራሱ መርጧልና አምላኩ ነው፤ ዘፍ 17፤8
  2. የተገረዙት የእግዚአብሔር ህዝቦች ናቸውና ክፋትንም ከህይወታቸው ማስወገድ አለባቸው፤ ዘጸ 10፤16
  3. እግዚአብሔር በእምነት ስለተቀበላቸው የጽድቃቸው መሠረት ነው፤ ሮሜ 4፤11

ሆኖም በሐዲስ ኪዳን ሥርዓት ሣይሆን፤ የሚያድነው የእግዚአብሔር ህግ መሆኑን ቅዱስ ጳውሎስ ያብራራል።ሮሜ 2፤25 ዋናው ነገር የሥጋ ሸለፈት መገረዝ ሳይሆን የልብ መለወጥና በእግዚአብሔር ማመን ሕጉንም መፈጸም ነው፣ ሲል ቅዱስ ጳውሎስ ምዕመናኑን በመንፈስ የተገረዙ መሆናቸውንም ጨምሮ አብራርቷል።ፊሊጵ 3፤30 በተለይም ህዝብና አህዛብ ማለትም ትንቢት የተነገረላቸው፣ ተስፋ የተነገራቸው እስራኤላውያን እና ከአህዛብ ወገን የመጡት ሁለቱም የክርስትና አማኞች በግዝረት ምክንያት ያስነሱትን አለመግባባት አስመልክቶ በጻፈው መልእክቱ በሐዲስ ኪዳን ዘመን ጥምቀት በግዝረት ፋንታ መተካቱን ያስረዳል።ቆላ 2፤11 ግዝረትም አሁን አይጠቅምም ይለናል። ገላ 5፤6።

ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግዝረት ስንመለስ ደግሞ፤ በመግቢያው እንደተገለጸው ኦሪትና ነቢያትን ልፈጽም እንጂ ልሽራቸው አልመጣሁም እንዳለ፤ ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና እርሱ ራሱ ሥርዓቱን ለመፈጸም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ በስምንተኛው ቀን እናቱ ወደ ቤተ መቅደስ ወስዳው ሊገረዝ በታሰበ ጊዜ በፍጡራን እጅ አልተገረዘም። ምላጩ በገራዡ እጅ እንዳለ ውኃ ሆኖ ተገኝቷል (መጽሐፈ ስንክሳር ጥር ስድስት)።ይህም በመለኮታዊ ኃይሉ ነው። እርሱም በግብር መንፈስ ቅዱስ ተገርዞ ተገኝቷል።ይህንንም ያደረገው ሰውን ንቆ ስርዓቱንም ጠልቶ ሳይሆን ደመ መለኮቱ ያለ ዕለተ ዓርብ የማይፈስ ስለሆነ እርሱ ባወቀ ይህን አደረገ ስሙንም አስቀድሞ በመልአኩ እንደተነገረ ኢየሱስ አሉት። ሉቃ 2፤21

በዚህም ምክንያት ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የግዝረት በዓል በየዓመቱ ጥር 6 ቀን ታከብራለች (መጽሐፈ ስንክሳር ጥር ስድስት)። ስታከብርም በግዝረቱ እለት የተፈጸሙትን ተአምራት በማስተማርና በማሳወቅ ነው።

ለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ምስጋና  ይሁን! አሜን!

ርእሰ ደብር ብርሃኑ አካል

 

ሰንበት ዘብርሃን

ሰንበት ዘብርሃን

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

ነአምን ክልኤተ ልደታተ እንዳሉ አባቶቻችን በሃይማኖተ አበው፤ ቅድመ ዓለም ከእግዚአብሔር አብ ያለ እናት፣ አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ የተወለደ፣ ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው የአብ አካላዊ ቃል ፤ ድኀረ ዓለም ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ያለ አባት፣ መለወጥ ሳያገኛት ዘር ምክንያት ሳይሆን፣ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ሰው የሆነ ፤ ወልደ እግዚአብሔር በመለኮቱ ወልደ ማርያም በትስብእቱ ፤ የሚባል ጌታ በተዋሕዶ ከበረ ብለን የቀናች የአባቶቻችን ሃይማኖታቸው ተዋሕዶን እንመሰክራለን፡፡

ስንዱዋ እመቤት ቤተክርስቲያናችን ወራትን እና ዘመናትን ከፍላ ነገረ ሃይማኖትን ታስተምራለች።አባቶቻችንም የወራቱንና የቀናቱን  የሰንበታቱንም ምስጢር በማገናዘብ የመጽሐፍ ቅዱስን ምንባባት ከቅዱስ ያሬድ መዝሙር ጋር በማዛመድ ግጻዌ የሚባልን መጽሐፍ ሰርተውልናል።

መዝሙር ዘብርሃን

በግጻዌ ዘሰናብት ከታኅሣሥ ፲፬  እስከ ታኅሣሥ ፳  ባሉት ቀናት ውስጥ ያለውን ሰንበት ብርሃን እንደሚባልና መዝሙሩም “ዘብርሃን አቅዲሙ ነገረ በኦሪት”የሚለው እንደሆነ አባቶቻችን ሠርተውልናል፡፡

ይህም የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ነገረ ሥጋዌን ነገረ ድኅነትን በውስጡ የያዘ ነው። ቅዱስ ያሬድ እንደ ንብ ነው፤ንብ ከመልካም አበባ ሁሉ እንዲቀስም ቅዱስ ያሬድም ከኦሪቱ ከነቢያቱ ከሐዲሳቱ እየጠቀሰ መጥኖ ማር የሆነውን ቃለ እግዚአብሔር አዘጋጅቶልናል፡፡

“ዘብርሃን አቅዲሙ ነገረ በኦሪት ከመ ይመጽእ ወልድ በስብሐት ዘይዜንዋ ለጽዮን ቃለ ትፍሥሕት”

ቃለ ትፍሥሕት የደስታ ቃልን አንድም ደስ የሚያሰኝ የምስጋና ቃልን፣ ለጽዮን ለሕዝበ ፳ኤል  የሚነግራት፣ ወልድ በክብር በምስጋና ለተዋሕዶ ለድኅነተ ዓለም ፣ ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም እንደሚመጣ  አስቀድሞ በኦሪት ተነገረ ይለናል ሊቁ ቅዱስ ያሬድ፡፡

አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው እንደሚሆንና እኛን እንደሚያድነን አስቀድሞ በኦሪት የተነገረውን ሲያስታውሰን ነው ፡፡ ለአብነትም  “አዳም መልካምንና ክፉን ለማወቅ ከእኛ እንዳንዱ ሆነ” ዘፍ  ፫፥፳፪ ተብሎ የተነገረው የወልደ እግዚአብሔርን ሰው መሆን የሚያሳይ ነው፡፡

“ወካዕበ ይቤ በአፈ ዳዊት ቡሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር ”

ዳግመኛ ምስክርነቱ የታመነ አምላክ እንደልቤ ብሎ ባከበረው በቅዱስ ዳዊት አንደበት “በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው” መዝ ፻፲፯፥፳፮ አለ ይለናል ሊቁ  ቅዱስ ያሬድ፡፡ በስመ እግዚአብሔር፦ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ በእግዚአብሔር ስም ፤በስምዐ እግዚአብሔር፦ እግዚአብሔር አብ መስክሮለት የመጣ ወልደ እግዚአብሔር ጌታ የባሕርይ አምላክ ነው፡፡ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትን በአፈ ዳዊት እያለ ትንቢቱን ምስክርነቱን ያነሳዋል ፡፡ አባቶቻችንም ከልደተ ዳዊት እስከ ፍልሰተ ባቢሎን ያለውን ፲፬ ትውልድ በሰንበት ዘብርሃን ያስቡታል፡፡

“ብርሃን ዘመጽአ ውስተ ዓለም ዘያበርህ ላዕለ ጻድቃን”

ቅዱስ ያሬድ ወልደ እግዚአብሔርን ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም የመጣው ብርሃን ዘበአማን፤  የዚህ ዓለም ጠፈር ደፈር የማይከለክለው መዓልትና ሌሊት የማይፈራረቅበት እውነተኛ ብርሃን፤ ለጻድቃን የሚያበራ ብሎ ይገልጠዋል፡፡ ይህም ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌል የመሰከረው ሊቃውንቱ እነ ቅዱስ ኤፍሬም በእመቤታችን ውዳሴ ላይ ያመሰጠሩት ነው፡፡

“መርዓዊሃ ለቤተ ክርስቲያን”

ቅዱስ ያሬድ ወልደ እግዚአብሔርን የቤተክርስቲያን ሙሽራ ብሎ ይገልጠዋል፡፡አካል የሌለው ራስ እንደሌለ ፥ ሙሽሪት የሌለችውም ሙሽራ የለም ። አካል፥ ሙሽሪት ያላት ቤተክርስቲያንን ሲሆን ራስ፥ ሙሽራ የተባለው ደግሞ ክርስቶስ ነው።ይህንም ቅዱስ ጳውሎስ “ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደ ሆነ እርሱም አካሉን የሚያድን እንደ ሆነ ባል የሚስት ራስ ነውና” ብሎ ገልጦታል ኤፌ ፭፥፳፫

“ይርዳእ ዘተኀጒለ ያስተጋብእ ዝርዋነ መጽአ ኀቤነ”

ከ፻ በጎች መካከል የጠፋውን አዳምንና ልጆቹን ይረዳ ይፈልግ ዘንድ፣ የተበተኑትን ይሰበስብ ዘንድ ከወዲያ ዓለም ወደዚህ ዓለም ወደ እኛ መጣ ፡፡

ምስባክ ዘብርሃን መዝ ፵፪፥፫


‹‹ፈኑ ብርሃነከ ወጽድቀከ

እማንቱ ይምርሓኒ ወይሰዳኒ ደብረ መቅደስከ

ወውስተ አብያቲከ እግዚኦ  ››

 

ፈኑ ብርሃነከ ወጽድቀከ

 

  • (ብርሃነከ) ብርሃን የተባለ ወልድን (ወጽድቅከ) መንፈስቅዱስን ላክልኝ
  • ብርሃነ ረድኤትህን አንድም ዮሴዕ ዘሩባቤልን ቂሮስ ዳርዮስን ላክልኝ
  • (ብርሃነከ) ሐዋርያትን (ወጽድቅከ) ሰብአ አርድእትን ላክልኝ
  • (ብርሃነከ) መስቀልን (ወጽድቅከ) ቀኖትን  ላክልኝ
  • (ብርሃነከ) ሥጋውን (ወጽድቅከ) ደሙን ላክልኝ

 

እማንቱ ይምርሓኒ ወይሰዳኒ ደብረ መቅደስከ

 

ብርሃን  የተባለ ወልደ እግዚአብሔርን በሐዋርያት በሰብአ አርድእት ትምህርት አምነን ሥጋውን ደሙን ተቀብለን መከራ መስቀሉን አስበን ወደመንግስቱ እንገባለንና እሊህ መርተው መመስገኛህ ወደምትሆን ወደ ኢየሩሳሌም ይውሰዱኝ ዘንድ ይላል ኅሩይ ቅዱስ ዳዊት


ወውስተ አብያቲከ እግዚኦ

እነሱ መርተው ወደ ገነት ወደ መንግሥተ ሰማያት ያግቡኝ።አብያት ብሎ መንግስተ ሰማያትን በብዙ ቁጥር ይናገራል።በብዙ ወገን በድንግልና፣ በሰማዕትነት፣ በብሕትውና አንድም በብዙ ማዕረግ በ፴፣ በ፷፣ በ፻ የምትወረስ ስለሆነ ነው።አንድም በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ እንዳለው በብዙ ተናገረ

በብርሃን የሚነበቡ ምንባባት

 

በሰንበት ዘብርሃን የሚነበቡ ምንባባት በዕለቱ መዝሙር ‹‹ዘብርሃን አቅዲሙ ነገረ በኦሪት›› ብርሃን ዘበአማን የተባለው እውነተኛው የዓለም ብርሃን ክርስቶስ ለሰው ልጆች ድኅነት ወደዚህ ዓለም እንደሚመጣ በኦሪት በነቢያት አስቀድሞ መነገሩን የሚያበስሩ የልደተ ክርስቶስን ዋዜማ የሚያስታውሱ ናቸው

 

    • ሮሜ  ፲፫ ፲፩ ፡ ፲፬ ‹‹ከእንቅልፍ የምትነሡበት ሰዓት አሁን እንደ ደረሰ ዘመኑን እወቁ፤ ካመንንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን ዛሬ ወደ እኛ ቀርቦአልና።ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል። እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር እንልበስ።በቀን እንደምንሆን በአገባብ እንመላለስ፤ በዘፈንና በስካር አይሁን፥ በዝሙትና በመዳራት አይሁን፥ በክርክርና በቅናት አይሁን፤ነገር ግን ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን ልበሱት፤ ምኞቱንም እንዲፈጽም ለሥጋ አታስቡ።….››

 

  • ፩ኛ ዮሐ ፩ ፥ ፩፡፲ ‹ስለ ሕይወት ቃል ከመጀመሪያው የነበረውንና የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን የተመለከትነውንም እጆቻችንም የዳሰሱትን እናወራለን፤ሕይወትም ተገለጠ አይተንማል እንመሰክርማለን፥ ከአብ ዘንድ የነበረውንም ለእኛም የተገለጠውን የዘላለምን ሕይወት እናወራላችኋለን፤እናንተ ደግሞ ከእኛ ጋር ኅብረት እንዲኖራችሁ ያየነውንና የሰማነውን ለእናንተ ደግሞ እናወራላችኋለን። ኅብረታችንም ከአባት ጋር ከልጁም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ነው።ደስታችሁም እንዲፈጸም ይህን እንጽፍላችኋለን።ከእርሱም የሰማናት ለእናንተም የምናወራላችሁ መልእክት። እግዚአብሔር ብርሃን ነው ጨለማም በእርሱ ዘንድ ከቶ የለም የምትል ይህች ናት።ከእርሱ ጋር ኅብረት አለን ብንል በጨለማም ብንመላለስ እንዋሻለን እውነትንም አናደርግም፤ነገር ግን እርሱ በብርሃን እንዳለ በብርሃን ብንመላለስ ለእያንዳንዳችን ኅብረት አለን፥ የልጁም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል።ኃጢአት የለብንም ብንል ራሳችንን እናስታለን፥ እውነትም በእኛ ውስጥ የለም።በኃጢአታችን ብንናዘዝ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው።ኃጢአትን አላደረግንም ብንል ሐሰተኛ እናደርገዋለን ቃሉም በእኛ ውስጥ የለም።››
  • የሐዋ ፳፮ ፥፲፪ ፡ ፲፱ ‹‹ስለዚህም ነገር ከካህናት አለቆች ሥልጣንና ትእዛዝ ተቀብዬ ወደ ደማስቆ ስሄድ፥ንጉሥ ሆይ፥ በመንገድ ሳለሁ እኩል ቀን ሲሆን በዙሪያዬና ከእኔ ጋር በሄዱት ዙሪያ ከፀሐይ ብሩህነት የበለጠ ብርሃን ከሰማይ ሲበራ አየሁ

 

ሁላችንም በምድር ላይ በወደቅን ጊዜ። ሳውል ሳውል፥ ስለ ምን ታሳድደኛለህ የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል የሚል ድምፅ በዕብራይስጥ ቋንቋ ሲናገረኝ ሰማሁ።እኔም  ጌታ ሆይ፥ ማንነህ አልሁ እርሱም አለኝ። አንተ የምታሳድደኝ እኔ ኢየሱስ ነኝ።ነገር ግን ተነሣና በእግርህ ቁም፤ ስለዚህ እኔን ባየህበት ነገር ለአንተም በምታይበት ነገር አገልጋይና ምስክር ትሆን ዘንድ ልሾምህ ታይቼልሃለሁና።የኃጢአትንም ስርየት በእኔም በማመን በተቀደሱት መካከል ርስትን ያገኙ ዘንድ፥ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሰይጣንም ሥልጣን ወደ እግዚአብሔር ዘወር እንዲሉ ዓይናቸውን ትከፍት ዘንድ፥ ከሕዝቡና ወደ እነርሱ ከምልክህ ከአሕዛብ አድንሃለሁ።ንጉሥ አግሪጳ ሆይ፥ ስለዚህ ከሰማይ የታየኝን ራእይ እምቢ አላልሁም››

 

ወንጌል ዘብርሃን ዮሐ ፩፥፩ – ፲፱



‹‹በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ።ይህ በመጀመሪያው በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ።ሁሉ በእርሱ ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም።በእርሱ ሕይወት ነበረች፥ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች።

ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም።ከእግዚአብሔር የተላከ ስሙ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤ሁሉ በእርሱ በኩል እንዲያምኑ ይህ ስለ ብርሃን ይመሰክር ዘንድ ለምስክር መጣ።ስለ ብርሃን ሊመሰክር መጣ እንጂ፥ እርሱ ብርሃን አልነበረም።ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበር።በዓለም ነበረ፥ ዓለሙም በእርሱ ሆነ፥ ዓለሙም አላወቀውም።የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም።ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም።ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን።

ዮሐንስ ስለ እርሱ መሰከረ እንዲህም ብሎ ጮኸ። ከእኔ በኋላ የሚመጣው እርሱ ከእኔ በፊት ነበረና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፤ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነበረ።እኛ ሁላችን ከሙላቱ ተቀብለን በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጥቶናልና ሕግ በሙሴ ተሰጥቶ ነበርና፤ጸጋና እውነት ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ሆነ። መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው።አይሁድም አንተ ማን ነህ ብለው ይጠይቁት ዘንድ ከኢየሩሳሌም ካህናትንና ሌዋውያንን በላኩበት ጊዜ፥ የዮሐንስ ምስክርነት ይህ ነው››

 

በትርጓሜ ወንጌል አባቶቻችን ይህን ስለ መለኮታዊ የሕይወት ቃልና ስለ ዮሐንስ መላክ የሚያትተውን ምንባብ በሰፊው አምልተው አመስጥረው ጽፈው አስቀምጠውልናል።

  • በቅድምና ስለነበረው ቃል ሲያብራሩ፦ ተጠመቀ ለማለት ተወለደ ማለት ጥንቱ ነው፤ተወለደ ለማለት ተፀነሰ ማለት ጥንቱ ነው፤ተፀነሰ ለማለት በቅድምና ነበረ ማለት ጥንቱ ነው።ያ ቃል ከስነፍጥረት አስቀድሞ የነበረ እግዚአብሔር ወልድ እንደሆነ ሲያስረዳም ያም ቃል ስጋ ሆነ ብሎ ያመጣዋል።ልብ እስትንፍስ ቀድመውት ወደኋላ የሚገኝ ቃል የለምና ቅድስት ሥላሴ አባት በመሆን አብ ወልድን አይቅድመውም አይበልጠውም፤ ወልድም መንፈስቅዱስን አይበልጠውም አይቀድመውም ፤ሦስቱ ስም አንዱ እግዚአብሔር ነው ብሎ አባ ሕርያቆስ እንደተናገረ አሐቲ ቅድምናሆሙ ለሥላሴ ወዕሩያን እሙንቱ በቅድምና እንዲል የቅድስት ሥላሴ ቅድምና አንድ የሆነ የተካከለ ቅድምና ነው።
  • ስለ ዮሐንስ መላክ ሲያብራሩ፦መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የብርሃንን ነገር ይመሰክር ዘንድ የመጣ እንጂ እራሱ ብርሃን አይደለም፤ሰው ሁሉ ብርሃን በተባለ ክርስቶስ ያምን ዘንድ የሚናገር፤በጨለማ በድንቁርና፣ በቀቢጽ ተስፋ በሞት ጥላ ውስጥ ሁሉ ለሚኖር ዓለም ፣ ዕውቀትን የሚገልጥ ጨለማን የሚያርቅ፣ ምትን ድል አድርጎ ተስፋ መንግስተ ሰማያትን የሚሰጥ  መሆኑን መስክሯል።

 

ማቴ ፭፥፲፮ ‹‹መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ››በጎ ሥራችሁን አይተው ሰማያዊ አባታችሁን እንደነርሱ  አርአያ የሚሆኑ የትሩፋት አበጋዝ ያስነሳልን አምላካችን ብለው እንዲያመሰግኑት ብርሃን በጎ ሥራችሁ ይገለጥ ብሎ ቅዱስ መጽሐፍ ያስተምረናል።ብርሃን ዘበአማን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃን ዕውቀትን በጎ ምግባርን ያድለን በብርሃን የምንመላለስ የብርሃን ልጆች ያድርገን  ወንድማችን የምናሰናክል ሳይሆን ለሌላው አርአያ የምንሆን ያድርገን።

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በኩረ ፍሥሐ ቀሲስ ኃይለኢየሱስ ተመስገን

 

ክብረ ክህነት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ክብረ ክህነት

ክፍል አንድ፡  አጀማመሩና ሥርዓቱ

ክህነት ተክህነ ካለው የግእዝ ቃል የወጣ፣የተገኘ ቃል ሲሆን አገለገለ ማለት ነው።መሥዋዕት ፣ጸሎት ልመና ወደ እግዚአብሔር እያቀረቡ ሰውና እግዚአብሔርን ማስታረቅ፣ እግዚአብሔር አምላክ ይቅር እንዲል ዘወትር በመሥዋዕቱ ፊት እየቆሙ መጸለይ ምሕረትን ፣ይቅርታን ከእግዚአብሔር ማሰጠት፤ ህዝቡ ደግሞ ኃጢአት እንዳይሠሩ ፣ሕገ እግዚአብሔርን እንዳይተላለፉ መምከር፣ማስተማር፣መገሰጽ መቻል ሲሆን በአጠቃላይ ክህነት ማለት በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የቆመ ምሰሶ፣ መሰላል ወይም ድልድይ ማለት ነው። ሰውና እግዚአብሔር ይገናኙበታልና።

የክህነት አገልግሎት የተጀመረው ዓለም ከመፈጠሩ በፊት ነው።ዓለም የሚለው ቃል በራሱ ብዙ ትርጉም ያለው ሲሆን በአንድ በኩል የሰው ልጅ እራሱ ዓለም ይባላል። ሊቁ ቅዱስ ያሬድ፤ “ኢኃደጋ ለምድር እምቅድመ ዓለም ወእስከ ለዓለም እንበለ ካህናተ ወዲያቆናት…” እግዚአብሔር አምላክ ዓለምን ከመፍጠሩ በፊትም ሆነ ከፈጠረ በሁዋላ ምድርን ያለካህናትና ዲያቆናት አልተዋትም ማለት ነው። በሥነ-ፍጥረት ቅደም ተከተል መሠረት የሰው ልጅ ከመፈጠሩ በፊት ቅዱሳን መላእክት እንደተፈጠሩ እና የክህነት አገልግሎትን እንደጀመሩ እንረዳለን። በመጽሐፈ ቅዳሴም፤ “እምቅድመ ይፍጥር መላእክተ ለቅዳሴ ኢተጸርአ ስብሐተ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ” ሲል መላእክትን እንኳን ለምስጋና ከመፍጠሩ በፊት በአንድነት በሦስትነት መመስገኑ በባህርይው ያልተቋረጠ መሆኑን ነው የሚያስረዳን።

ወደ ሰው ልጅ የክህነት አገልግሎት ስንመጣ ደግሞ በሦስት አበይት ክፍላተ ዘመን መድበን ማየት እንችላለን። በዘመነ ሕገ ልቡና፣ በዘመነ ብሉይ ኪዳን እና በዘመነ ሐዲስ ኪዳን ብለን።

ክህነት በህገ ልቦና፤ የቤተሰብ ክህነት በመባል ይታወቅ ነበር። ምክንያቱም መሥዋዕቱ የሚሰዋው፣ ጸሎቱ የሚጸለየው፣ ልመናው፣ሥርየቱ ስለቤተሰብ ብቻ ስለነበረ ነው። ለዚህም መነሻው አባታችን አዳም ራሱ ሕገ እግዚአብሔርን በመተላለፍ ዕፀ በለስን በልቶ፣ኃጢአት ሠርቶ፣ ከገነት በወጣና ከፈጣሪው በተለየ ጊዜ ንሰሐ ገብቶ፣ መሥዋዕት ሠውቶ፣ ወደፈጣሪው ባመለከተ ጊዜ ንሰሐን የሚቀበል እግዚአብሔር ንስሐውን ተቀብሎ የተስፋውን ቃል ሰጠው። ይህም ቃል “በሐሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እተወለድ እምወለተ ወለትከ…” አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ፤ ህፃን ሆኜ፣ በምድርህ ተመላልሼ፣ በመስቀል ላይ በዕለተ ዐርብ ተሰቅዬ በሞቴ አድንኃለሁ የሚለው ነው። ይህም ቃል በመጽሐፈ ቀሌምንጦስ በመጀመርያው ክፍል የሚገኘው ሲሆን ቅዱስ ያሬድም በድጓው በዜማ እያዋዛ፣ እያቀነባበረ በተደጋጋሚ ሲያመሰጥረው እናገኛለን።

ኢዮብም ምናልባት ልጆቼ እግዚአብሔርን በልባቸው ሰድበው ይሆናል ብሎ ይልክና ይቀድሳቸው ነበር። ኢዮብም ማልዶ ተነስቶ እንደቁጥራቸውም ሁሉ የሚቃጠል መሥዋዕት አቀረበ እንደሁ ኢዮብ ሁልጊዜ ያደርግ ነበር። ኢዮ 1፣ 5። ጻድቁ ኖኅም ከማየ አይህ በሁዋላ መሥዋዕት እንደሠዋ እና እግዚአብሔር የገባለትን ቃል ኪዳን መሐላውንም በቀስተ ደመና ምልክት እንዳጸና ይህችም ቀስተደመና የድንግል ማርያም ምሳሌ መሆኗን ኢትዮጰያዊው ሊቅ አባ ጽጌ ድንግል “ቀስተደመና ማርያም ትዕምርተ ኪዳኑ ለኖኀ ዘእግዚአብሔር ሤመኪ ለተዝካረ ምሕረተ ወፍትህ…” እግዚአብሔር ለዓለም ድኀነት ያቆማት የቀስተደመናዋ ምሳሌ ድንግል ማርያም አንቺ ነሽ፤ እግዚአብሔር ለምሕረትና ለፍርድ ሹሞሻልና ሲል ነው።

አበ ብዙኀን አብርሃም ከሚታወቅባቸው በጎ ሥራዎቹ አንዱ ሁል ጊዜ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት በማቅረቡ ነው።በዚህም ከመሥዋዕት ሁሉ የሚበልጠውን አንድ ልጁን ይስሐቅን ሳይቀር በቆራጥነት ለመሥዋዕት እንዳቀረበ እናያለን። በዚህ ሥራውም የእግዚአብሔር ወዳጅ ተባለ። በሕገ ልቦና ሁሉም አባቶች መሥዋዕት ለማቅረብ ባለድርሻ ቢሆኑም ከዚህ በላይ የተጠቀሱት ምሳሌ ናቸው።እዚህ ላይ ለየት ያለው ሌላው ክህነት የመልከጼዴቅ ክህነት ነው። ይህ የአዲስ ኪዳን ምሳሌ ሲሆን እራሱ መልከጼዴቅም የክርስቶስ ምሳሌ ነው። ከላይ እንደተጠቀሰው የሕገ ልቦና ክኅነት የቤተሰብ ክኅነት የተባለበት ምክንያት መሥዋዕቱ ለራሱና ለቤተሰብ ብቻ እንጂ ሌላውን የሚያካትት መሥዋዕት፣ ጸሎት ልመና ባለመሆኑ ነው። ብዙኃኑን አለማካተቱ ብቻ ሳይሆን የሚያስገኘውም ሥርየት ጊዜያዊ ሥርየት ማለትም ከአባር፣ ከቸነፈርና ከመቅሠፍት የሚያድን ሥጋዊ ድኀነት ብቻ እንጂ ነፍሳዊ ድኀነትን የማያካትት በመሆኑ ነው።

ክህነት በብሉይ ኪዳን፤  ከአሥራ ሁለቱ የያዕቆብ ልጆች በነገደ ሌዊ የተላለፈ ሲሆን የቤተሰብ መሆኑ ቀርቶ የነገድ ክህነት መሆኑን እናያለን። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስረዳን ይህ ሥርዓት የተጀመረው በእግዚአብሔር ወዳጅ በሙሴ አማካይነት ሲሆን ሙሴ ቀጥታ ከእግዚአብሔር በመነጋገር የመሠረተው ስለሆነ ሕጉ፣ሥርዓቱ ከእግዚአብሔር የተሰጠ እንጂ ሰው ሠራሽ ባለመሆኑ እስከ ሐዲስ ኪዳን ዘመን ድረስ አገልግሎአል። ካህናቱም ከመሥዋዕት፣ጸሎት፣ ተግሣጽና ምክር በተጨማሪ ትንቢት የመናገር ሀብት ያላቸውም ነበሩ። ከእነዚህም ነገሥታት፣ ነብያት፣ መሣፍንት ይገኙበታል። በዚህ ዘመን ውስጥ ግን ክህነቱ ተሰጥቶአቸው ድርሻቸውን በአግባቡ የተወጡ ብዙዎች ሲሆኑ ባለመወጣታቸው እና ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን ክህነት ባለመጠበቃቸው የተቀጡም አሉ። ለምሳሌ የኤሊ ልጆች አፍኔ እና ፊንሐስ እራሳቸው እነደጠፉ ታቦተ ሕጉንም እንዳስማረኩ ህዝቡንም እንዳጠፉና እንዳዋረዱ እናያለን። ክህነት ሳይፈቀድላቸው በጉልበት፣ በትምክሕት ተነሳሥተው ለማገልገል ሞክረው የጠፉም አሉ። በሙሴና በአሮን ዘመን የነበሩ ዳታን አቤሮን ሌሎችም ይጠቀሳሉ።

ክህነት በሐዲስ ኪዳን፤ ደግሞ የተመሠረተው በራሱ በባለቤቱ በጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። “ለሊሁ ሠዋዒ ወለሊሁ ተሠዋዒ” ቅዱስ ጳውሎስ በዕብራውያን ምልእክቱ እንዳስተማረን እራሱ መሥዋዕት እራሱ ካህን (የመሥዋዕቱ አቅራቢ) ሆኖ ነው ያዳነን። ዕብ ፲፣፲፪ ይህም ክህነት የእርሱ የባህርይው ሲሆን ለቅዱሳን ሐዋርያት ደግሞ ጸጋውን በመሥጠት ከእነርሱ ቀጥሎ በእነርሱ ለሚተካ አምኖ፣ ተጠምቆ፣ ተምሮ እንዲሁም ሕጉን፣ ትዕዛዙን፣ ሥርዓቱን ጠብቆ ለተገኘ ሁሉ ትምህርቱ፣ እምነቱና ትህትናው እየታየ ዘር፣ቀለም፣ቋንቋ፣ነገድ፣ ሥልጣን ፣ሀብት፣ ቦታ ሳይለይ ሁሉም መሾም እንደሚችሉ ሥልጣን ሰጠ። ይህ ሥልጣን እስከ ዓለም ፍጻሜ የማሠር፣የመፍታት፣ መንግሥተ ሰማያትን የመዝጋትና የመክፈት ሥልጣን፣ ይቅር ላላችሁዋቸው ይቅር እላቸዋለሁ፤ይቅር ላላላችሁአቸው ግን ይቅር አልላቸውም የተባለልን ቅዱስ ጴጥሮስን ትወደኛለህ ብሎ ሦስት ጊዜ በመጠየቅ በጎቼን ጠብቅ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ፣ ግልገሎቼን ጠብቅ ያለበት የመጠበቅ የማሠርና የመፍታት፣ ይቅር የማለት ሥልጣን ነው። መናዘዝ ማለት በኃጢያቱ ተጸጽቶ ከእግዚአብሔር ይቅርታን ለማግኘት ወደ ካህን የቀረበን ተነሳሂ፤ ንሥሐን ሰጥቶ በንሥሐ ሥርየት ወደ አምላክ ማቅረብ ማለት ነው።

ይህ ክህነት ለህዝብ፣ ለአህዛብ ሁሉ፣ እንዲሁም ለአመነ፣ ለተጠመቀና ለተማረ ሥለተፈቀደ፡ ክህነተ ብዙኃን ይባላል። አሰጣጡ ግን ሕግና ሥርዓት አለው። ከቅዱሳን ሐዋርያት ተያይዞ የመጣ በመሆኑ የነሱ ተተኪዎች በሆኑት በብጹአን ሊቃነ ጳጳሳት ካልሆነ በቀር በሌላ አይሠጥም ወይንም አይሰየምም።

ይቆየን!

ርእሰ ደብር ብርሃኑ አካል

ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ምንድን ነው?

፩. ሥርዓት ምንድን ነው?
 
ሥርዓት “ሠርዐ” ሠራ ከሚለው የግዕዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙም ደንብ፣ አሠራር፣ መርሐ ግብር ማለት ነው። ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ስንልም የቤተ ክርስቲያን ዕቅድ፣ የቤተ ክርስቲያን አሠራር መርሐ ግብር ወይንም ደንብ ማለታችን ነው።
 
ሥርዓት የሚከተሉት ጥቅሞች አሉት፦
·        ሥራን ወጥ በሆነ መልኩ ለመፈጸም

ማንኛውንም ነገር ወጥና ዘላቂ በሆነ መልኩ ለመሥራት ከየት ተጀምሮ በየት በኩል ሄዶ በየት በኩል እንደሚጠናቀቅ ወጥ የሆነ የአሠራር ሥርዓት ይዘጋጅለታል። የአንድ ሥራ አሠራር በትክክል ካልተነደፈና አካሄዱ ካልተስተካከለ፤ ሥራው የተዘበራረቀ ይሆናል ፍጻሜውም አያምርም።

·        አንድ ሃሳብና አንድ ልብ ለመሆን

አንድ መሥሪያ ቤት በመሥሪያ ቤቱ ውስጥ ያሉ ሠራተኞች ተግባብተውና ተረዳድተው እንዲሠሩ ሥርዓት ሊኖረው ይገባል። ያ ሥርዓት ነው ሠራተኞቹን እንደመመሪያ ሆኖ ፈር እየቀደደ የሚመራቸውና የሚያስተዳድራቸው። ይህ ካልሆነ ግን እርስ በእርሷ እንደምትለያይ መንግሥት ሳይግባቡ ይቀሩና የመሥሪያ ቤቱንም ራዕይ ማሳካት ሳይችሉ ይቀራሉ። ለዚህ ነው በየአህጉራቱ፣ በየማኅበረሰቡ፣ በየማኅበሩ፣ በየቤተሰቡ የመተዳደሪያ ሥርዓት ማውጣት ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ የሆነው። እንደውም አንዳንድ መሥሪያ ቤቶች ሥራቸውን ከመጀመራቸው በፊት ሊኖራቸው ከሚገቡ ነገሮች መካከል ሥርዓት አንዱና ዋነኛው እንደሆነ ሲነገር ሁላችንም እንሰማለን።

ማኅበረ ምዕመናንም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንደጻፈው የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ አንድ ዓይነት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ያስፈልገናል። ብዙ ስንሆን አንድ ልቡና አንድ ሃሳብ የሚያደርገን ሥርዓት ነውና። /ኤፌ. ፬፥፫፤ የሐዋ. ፬፥፴፪፤ ሮሜ. ፲፭፥፮/።

·        የሃይማኖትን ምሥጢራት ለመጠበቅ
ሥርዓት የሃይማኖት መገለጫ ነው። ጥምቀት፣ ቁርባን፣ ጾም፣ ጸሎት፣ ሥግደት፣ ወዘተ በማመን ብቻ የሚያበቁ ሳይሆን የአፈጻጸምና አተገባበር መንገድ /ሥርዓት/ ያስፈልጋቸዋል። የእነዚህ ሁሉ ዝርዝር አፈጻጸም በሥርዓት ውስጥ ይካተታል። ስለዚህ በአንዲት ርትዕትና ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን እምነት ሥር ያሉ ሁሉ ያቺን አንዲት እምነት የሚገልጹት አንድ ዓይነት በሆነ ሥርዓት ነው። ሥርዓት በመሠረተ እምነት /ዶግማ/ የምናምናቸውን በተግባር የምንገልጽበትና ተግባራዊ የምናደርግበት መንገድ ስለሆነ ሥርዓቱ ሲሠራና ሲፈጸም ሃይማኖታዊ አንድምታና ነጸብራቅ ይኖረዋል።
  
፪. ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን
ቤተ ክርስቲያን ማለት ሕንፃው፣ የክርስቲያኖች አንድነት /ጉባኤ/ እና የምዕመኑ ሰውነት በመሆኑ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የምንለውም በእነዚህ በሦስቱ ላይ የተሠራውን ሥርዓት ነው። አንዳንዶቻችን ቤተ ክርስቲያንን ከራሳችን አርቀን ሌላ አካል አድርገን ስለምንመለከት ሥርዓቱ እኛን የሚመለከት አይመስለንም። ሥርዓቱ ግን የተሠራው ለሦስቱም የቤተ ክርስቲያን ትርጓሜዎች መሆኑን ማወቅ ተገቢ ነው።
ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ምንጩ ወይንም መሠረቱ መጽሐፍ ቅዱስ፣ የቅዱሳን አባቶቻችን ጉባኤያት ውሳኔ /ሲኖዶስ/ እና አባቶቻችን ሊቃውንት በተለያዩ ጊዜ ያደረጓቸው ጉባኤያት ውሳኔዎች ናቸው።
ሰንበትን ማክበር፣ በጻድቃን ስም አብያተ ክርስቲያናትን ማነጽ፣ የቁርባን ሥርዓት፣ የመሳሰሉት ከመጽሕፍ ቅዱስ የተገኙ ሥርዓቶች ናቸው። /ዘፍ. ፳፰፥፳-፳፪፤ ዘጸ. ፲፮፥፳፱፤ የሐዋ. ፩፥፲፪/።

ወደ ቤተ ክርስቲያን የገባውንና የተቀደሰውን ንዋየ ቅድሳት እንደገና ወደውጭ አውጥቶ ለሥጋዊ ጥቅም ማዋል እንደማይገባ /ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፩ ረስጣ ፳፰/፣ ጥምቀት በፈሳሽ ውኃ መፈጸም እንዳለበት፣ ወንዶች ሴቶችን ሴቶች ደግሞ ወንዶችን ክርስትና እንዳያነሱ፣ ሥጋ ወደሙ ለመቀበል ፲፰ ሰዓት መጾም እንደሚገባ፣ ሥጋ ወደሙ በምድር ላይ እንዳይወድቅ /እንዳይነጥብ/፣ ያላመኑ ሰዎች ሥጋ ወደሙን መቀበል እንደሌለባቸው፣ ወዘተ ያሉት ደግሞ በሲኖዶስ /የቅዱሳን አባቶቻችን ጉባኤያት/ የተገኙ ሥርዓቶች ናቸው።

ከእናቱ፣ ከእህቱ፣ ከአክስቱ ወይንም እንደዚህ ባለ ሁኔታ ከምትታሰብ ሴት ጋር ካልሆነ በቀር አንድ ኤጲስ ቆጶስ፣ አንድ ቄስ፣ አንድ ዲያቆን፣ ወይንም ሌላ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ከማንኛውም ሴት ጋር አብሮ እንዳይኖር፤ ስለ መናፍቃን ጥምቀት፣ ስለ ትንሣኤ በዓል አከባበር፣ ስለ ድንግልና ኑሮ፣ ወዘተ ደግሞ በተለያዩ ጉባኤያት አባቶቻችን ያስተላለፏቸው ውሳኔዎችና ቀኖናዎች የተገኙ ሥርዓቶች ናቸው።

የቤተ ክርስቲያን አመሰራረትና የቅዳሴ አገልግሎት ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አንጻር
 
መቼም በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን እየሰፋች ከሀገር ቤት አልፋ በውጭ ሀገርም አብያተ ክርስቲያናት እየታነጹ ስለሆነና ሁላችንም የቻልን ዘወትር ቅዳሴ በሚቀደስባቸው ዕለታት፣ ያልቻልን ደግሞ በዕለተ ሰንበት ለቅዳሴ ወደ ቤተ ክርስቲያን ስለምንሄድ ስለ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን አመሠራረት፣ አሠራርና ቡራኬ፣ እንዲሁም ስለ ሥርዓተ ቅዳሴ ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አንጻር እንዴት መሆን እንዳለበት እንገነዘባለን። ለዚህም እንዲረዳን እንደሚከተለው እናያለን።
 

ቤተ ክርስቲያን ስትሠራ

ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ ቃሉ ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል /ቤቴሰ ቤተጸሎት ትሰመይ/ የሚለው /ኢሳ. ፶፮፥፮-፯፤ ኤር. ፯፥፲፩፤ ማቴ. ፳፩፥፲፫፤ ማር.  ፲፩፥፲፯፤ ሉቃ. ፲፱፥፵፮፤ ዮሐ. ፪፥፲፮-፲፯/ ሲሆን ቤተ ክርስቲያን የዋዛ የፈዛዛ፣ የሳቅ የስላቅ፣ የጨዋታ፣ የመብል፣ የመጠጥ ቤት ሳትሆን፤ ምዕመናን ኃጢአት ቢሠሩ ሰለ ኃጢአታቸው የሚያዝኑባት የሚያለቅሱባት ንጹሕ የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ካህናት የሚያስተምሩባት፣ ምዕመናን የሚማሩባት የግል ጸሎት፣ የማኅበር ጸሎት የሚጸልዩባት፣ በኅብረት የሚያስቀድሱባት ሥጋ  ወደሙ የሚቀበሉባት፣ የኃጢአት ሥርየት የሚያገኙባት፣ ሕፃናት በአርባ ቀንና በሰማንያ ቀን በጥምቀተ ክርስትና አማካኝነት ከሥላሴ የጸጋ ልጅነት የሚቀበሉባት፣ ኢአማንያን የነበሩ በመምህራን ትምህርት አምነው ክርስቲያን የሚሆኑባት፣ ለክህነትም ሆነ ለአባልነት የዘር ሐረግ የማይቆጠርባት ዓለም አቀፋዊት የእግዚአብሔር ቤት ናት፡፡
 
አንዲት ቤተ ክርስቲያን ስትመሠረት ጀምሮ ሥርዓት አላት። የምትመሠረተው ባንድ ግለሰብ ስም ሳይሆን በካህናትና በምዕመናን ጥያቄ በሀገረ ስብከቱ ኤጲስ ቆጶስ ፈቃድና ትእዛዝ ነው፤ ካለኤጲስ ቆጶስ ፈቃድ ከመጽሐፉ ትዕዛዝ ወጥቶ አንዱ ቢያቋቁም ወይም ቢሠራ ቤተ ክርስቲያን ናት ብለው ለዘለዓለሙ በዛች ቤተ ክርስቲያን አይቁረቡባት፤ እንደገበያ፣ እንደእንስሳት በረት ፈት ሆና ትኑር ይላል። /ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፩-፫/።
 
ቤተክርስቲያን ለመሥራት ፈቃድ ከተገኘ በኋላ ስለ አሠራሯ የሚከተለው ሥርዓት ተሠርቶላታል። ቤተ ክርስቲያኗ ስትሠራ ደጆችና መስኮቶች አውጡላት ዛፍ ቅረጹላት ሐረግ ሳቡላት እንደሚል በተቻለ መጠን ሊያስጌጧት ይገባል የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ናትና።  በሰማይ ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት እንዲያበሩ፣ ሰባቱ ሰማያት ብሩሃን እንዲሆኑ ቤተ ክርስቲያንም ብርህት ትሁን፤ ይልቁንም ክቡራት መጻሕፍት ሐዲሳት፣ የጳውሎስ መልእክታት፣ የሐዋርያት መልእክታት፣ ግብረ ሐዋርያት በሚነበቡበት ጊዜ የበራች ትሁን፣ እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ ያለውም ይህንኑ ያመለክታል። /ማቴ. ፭፥፲፬/። ቅዱስ ወንጌል በሚነበብበት ጊዜ ግን ፈጽማ የበራች ትሁን፤ እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ ያለው ይሻል። /ዮሐ. ፱፥፭/።
 
ቤተ ክርስቲያን ስትባረክ
 
ቤተ ክርስቲያን ሕንፃዋ ተፈጽሞ በምትባረክበትና በምትቀደስበት ጊዜ ከኤጲስ ቆጶሱ ጋር ሰባት ቀሳውስት አብረውት ሊኖሩ ይገባል፣ ታቦቱም በሚባረክበት እንደዚሁ ሊሆን ይገባል፣ ኤጲስ ቆጶሱ እግዚአብሔር ሰውን የሚያከብርበት ራሱን የሚያስመስልበት ነውና ደስ በሚያሰኝ በቅብዐ ቅዱስ በሜሮን ያክብራት ያትማት፣ ታቦቱንም በመቅደስ ውስጥ በመንበር ያስቀምጡባት ከታቦቱ ጋራ የዮሐንስን ወንጌል ያኑሩ ከደቀ መዛሙርቱም በጌታ ኢየሱስ አጠገብ የሚቀመጥ ጌታ የሚወደው ቅዱስ ዮሐንስን ነበርና። /ዮሐ. ፲፫፥፳፫/ ።
 
ታቦቱም ሲቀረጽ ከላይ አልፋ፣ ቤጣ፣ የውጣ፣ ወኦ/ወዖ/ ይቀረጻል። ቀጥሎ እመቤታችንን፣ ከእመቤታችን ቀጥሎ ዮሐንስን፣ ቀጥሎ ቤተ ክርስቲያኑ የሚተከለው ታቦት መልአክም ቢሆን፣ ሰማዕትም ቢሆን፣ ጻድቅም ቢሆን ይቀረጻል። እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ካልተሟሉ ታቦቱን ሊቀድሱበት አይገባም።
 
ከቤተ ክርስቲያን የገባ ዕቃ የወርቅ፣ የብር፣ ፃሕል ጽዋእ እርፈ መስቀል ቢሆን ንዋየ ቅድሳት ነው ተብሎ አቡነ ዘበሰማያት ከተደገመበት በኋላ ከቤታቸው ወስደው በፃሕሉ ፈትፍተው ሊበሉበት በጽዋው ቀድተው ሊጠጡበት አይገባም። ደፍረው ቢያደርጉ ሥርዓት ማፍረስ ነውና ይህን ያደረገ ቢኖር በአንድ ሁለት ተቀጥቶ ንሰሐውን እሰኪፈጽም ከምዕመናን ይለይ። /ዳን. ፭፥፩-፴፩/።
 
በቤተ ክርስቲያንም ኤጲስ ቆጶሳት፣ ካህናት፣ ዲያቆናትና ምዕመናን እንዴት መቆም እንዳለባቸው ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚከተለው ይገልጻል። ኤጲስ ቆጶሳት የቤተ ክርስቲያን አዛዚያን እንደመሆናቸው በታቦቱ ፊት ይቁሙ፣ ቀሳውስትም መምህራን እንደመሆናቸው ከኤጲስ ቆጶሳት ቀጥለው ይቁሙ፣ ሊቀ ዲያቆናትም ከኤጲስ ቆጶስ አጠገብ ይቁሙ፣ ዲያቆናትም አገልጋዮች እንደመሆናቸው ከቀሳውስት ቀጥለው ይቁሙ፣ ከዲያቆናት ቀጥለው ሕዝቡ ሁሉ ባንድ ቦታ ይቁሙ፣ የሚበቃ ቦታ ቢኖር ሕፃናት በአንድ ወገን ለብቻቸው ይቁሙ፣ የሚበቃ ቦታ ከሌለ ግን ከአባቶቻቸው ጋራ ተስገው ይቁሙ፣ እንደዚሁም ሴቶች ባንድ ወገን /ቦታ/ ለብቻቸው ይቁሙ፣ ቦታ ቢገኝ ሕፃናት ሴቶች ባንድ ወገን ለብቻቸው ይቁሙ፣ ቦታ ባይኖር ግን ሕፃናቱ በፊት እናቶች በኋላ ይቁሙ፣ ደናግላን ሴቶችና ባልቴቶች ግን ከሴቶች በላይ ይቀመጡ ። /ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፪ ድስቅ ፲፪ ኒቅያ ፷፩/።
 
ሥርዓተ ቅዳሴ
 
በቅዳሴ ጊዜ ስለሚደረጉና ሰለማይደረጉ ነገሮች ደግሞ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚከተለው ያዝዛል፦
 
በቅዳሴ ጊዜ የሚስቅ ሰው ቅዱስ ባስልዮስ በጻፈው በ፸፪ኛው አንቀጽ ካህን ቢሆን የሚያቀብል ነውና ሥጋ ወደሙን ከተቀበለና ካቀበለ በኋላ ወጥቶ አንድ ሱባዔ ይቀጣ ይጹም ይስገድ፣ የሳቀው ሕዝባዊ ቢሆን ግን ሥጋ ወደሙን ሳይቀበል ያን ጊዜ ፈጥኖ ይውጣ ይላል። ምነው ፍርድ አበላለጠ ካህኑን ተቀብሎ ወጥቶ ይቀጣ አለ፤ ሕዝባዊውን ሳይቀበል ወጥቶ ይሂድ አለ ቢሉ ካህኑ የሚቆመው ከውስጥ ነው ሲስቅ የሚያየው የለም። ካህኑ በቅዳሴ ጊዜ ቅዳሴውን ጥሎ ወጥቶ ሲሄድ ባዩት ጊዜ ቄስ እገሌ አባ እገሌ በመሥዋዕቱ ምን አይተውበታል ብለው መሥዋዕቱን ሳይቀር ይጠራጠሩታል፤ ስለዚህ ነው። ምዕመኑ ግን ሲስቅ ሁሉ ያየዋልና ለሌላ መቀጣጫ እንዲሆን፤ በቤተ መቅደስ የማይወደድ ሌላ ነገር አይናገር፤ በቤተ መቅደስ ጭንቅ፣ ደዌ ሳያገኘው አንዱን ስንኳ ምራቁን እንትፍ አይበል። ነገር ግን ደዌ ቢያስጨንቀው ድምፅ ሳያሰማ ምራቁን በመሐረቡ ተቀብሎ ያሽሸው።
 
በቤተ ክርስቲያንና በቅዳሴ ጊዜ ማንም ማን ዋዛ ፈዛዛ ነገር የሚናገር አይኑር፣ ቤተ ክርስቲያን በፈሪሃ እግዚአብሔር ሆነው የሚጸልዩባት የጸሎት ቦታ ናትና ቅዳሴው ሳይፈጸም አቋርጦ መውጣት አይቻልም፣ አይፈቀድም፣ በጣም ጭንቅ ምክንያት ወይም በሕመም ምክንያት ከሆን ግን ክቡር ወንጌል ከተነበበ በኋላ ሊወጣ ይችላል። በቅዳሴ ጊዜ ካህናት የሚቀድሱባቸው አልባሳት ነጫጭ ይሁን ነጭ ልብስ ደስ እንዲያሰኝ በሥጋ ወደሙ የተገኘ ክብርም ደስ ያሰኛልና፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ባህርየ መለኮቱን በገለጸ ጊዜ ልብሱ እንደበረድ ነጭ ሆኗል። መላእክትም ወርኃ ሰላም ወርኃ ፍስሐ ነው ሲሉ የልደት፣ የትንሣኤ፣ የዕርገት ነጫጭ ልብስ ለብሰው ታይተዋል።
 
አንድ ሰው እንኳ ጫማ አድርጎ ከቤተ መቅደስ አይግባ ልዑል እግዚአብሔር የምትቆምባት ደብረ ሲና የከበረች ናትና ጫማህን አውልቅ ብሎ ለሙሴ ተነግሮታልና። /ዘጸአት ፫-፭/ ።
 
በቅዳሴ ጊዜ ተሰጥዖውን የማያውቅ ደግሞ በአንክሮ፣ በተዘክሮ፣ በአንቃእድዎ፣ በንጹሕ ልቡና፣ በሰቂለ ሕሊና ሆኖ ሕሊናው ወደ ዓለማዊ እንዳይወስደው መቆጣጠር አለበት።
 
ቅዱስ ወንጌል ከተነበበ በኋላ ካህኑ ለሕዝቡ ተርጉሞ ይንገራቸው ያስተምራቸው እጁንም በሚታጠብበት ጊዜ የተጣላችሁ ሳትታረቁ፣ የሰው ገንዘብ የወሰዳችሁትን ሳትመልሱ ሥጋ ወደሙን ብትቀበሉ ሥጋው እሳት ሆኖ ይፈጃችኋል ደሙ ባህር ሆኖ ያሰጥማችኋል። ነገር ግን የወሰዳችሁትን የሰው ገንዘብ መልሳችሁ፣ ከተጣላችሁት ታርቃችሁ ኃጢአት ብትሰሩ ንስሐ ገብታችሁ ብትቀበሉት ግን መድኃኒተ ሥጋ መድኃኒተ ነፍስ ይሆናችኋል። በረከተ ሥጋውን በረከተ ነፍሱን ያድላችኋል ብሎ ይንገራቸው ያስተምራቸው ይላል።
 
በቅዱስ ቁርባን ጊዜም አስቀድሞ ሊቃነጳጳሳት፣ ጳጳሳት፣ ኤጲስ ቆጶሳት ይቀበላሉ፤ ቀጥሎ በቁምስና መዓርግ ያሉ መነኮሳት፣ ቀጥሎ ቀሳውስት፣ ዲያቆናት ይቀበላሉ፤ ቀጥሎ ወንዶች በአርባ ቀን የሚጠመቁ ሕፃናት ከሁሉ አስቀድመው ይቀበሉ የዕለት ሹማምንት ናቸውና በንጽሐ ጠባይእ መላእክትን ይመስላሉና። ከነዚህ ቀጥሎ ከአርባ ቀን በኋላ እስከ ስድስት፣ ሰባት ዓመት ያሉት ሕፃናት ትንሾቹ በፊት እየሆኑ እንደየዕድሜያቸው ይቀበሉ፤ ከዚያ ቀጥለው /ክህነት የሌላቸው/ በድንግልና ኑረው የመነኮሱ ደናግል ይቀበሉ፤ ከዚያ ቀጥለው ሃያ፣ ሃያ ሁለት ዓመት የሆናቸው ደናግል ይቀበሉ፤ ከዚያ ቀጥለው በሹመት ያሉ ናቸውና ንፍቀ ዲያቆናት፣ አናጉንስጢሳውያን፣ መዘምራን ይቀበላሉ፤ ከዚያ ቀጥለው የንስሐ ሕዝባውያን በየመዓርጋቸው ይቀበላሉ።
 
በሴቶችም በኩል ከሁሉ አስቀድሞ የተጠመቁ የሰማንያ ቀን ሕፃናት ይቀበላሉ የዕለት ሹማምንት ናቸውና በንጽሐ ጠባይእ መላእክትን ይመስላሉና፤ ከነዚያ ቀጥሎ ከሰማንያ ቀን እስከ ስድስት፣ ሰባት ዓመት ያሉ ሕፃናት እንደየዕድሜያቸው ሕፃናቱ አስቀድመው ታላላቆች ቀጥለው ይቀበላሉ፤ ከዚያ ቀጥለው አሥራ ሁለት፣ አሥራ አምስት የሆናቸው ደናግል ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው የቀሳውስት ሚስቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው በሕግ ኑረው የመነኮሱ እናቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያው ቀጥለው የዲያቆናት ሚስቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው በንሰሐ ተመልሰው የመነኮሱ መነኮሳት እና መነኮሳይያትይቀበላሉ፤ ከነዚያ በኋላ የንፍቀ ዲያቆናት፣ የአናጉንስጢሳውያን፣ የመዘምራን ሚስቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው በሕግ ጸንተው ያሉ ሕጋውያን እናቶች ይቀበላሉ፤ ከነዚያ ቀጥለው የንስሐ ሕዝባውያን ሚስቶች በየመዓርጋቸው ይቀበላሉ።
 
ከዚህ በኋላ ካህኑ ሥጋ ወደሙን በፈተተበት እጁ ሕዝቡን ፊታቸውን ይባርካቸው። ቀሳውስት ግን እጅ በእጅ ተያይዘው እርስ በርሳቸው ይባረኩ። ቀዳሹ ካህን ቀሳውስትን ሲያሳልም “የጴጥሮስን ሥልጣን ባንተ አለ” ይበል፣ ተሳላሚው ቄስም “መንግሥተ ሰማያት ያውርስህ ከሾመ አይሻርህ” ይበል። ለዲያቆናትም “ልዑል እግዚአብሔር ያክብርህ ይባርክህ፣ ለማስተማር ዓይነ ልቡናህን ያብራልህ፣ ምሥጢሩን ይግለጥልህ” እያለ ይባርካቸው። ለምዕመናንም “ልዑል እግዚአብሔር ያክብርህ፣ ይባርክህ፣ ገጸ ረድኤቱን ይግለጽልህ” እያለ ይባርካቸው። ለሴቶችም “ልዑል እግዚአብሔር ይባርክሽ፣ ያክብርሽ ገጸ ረድኤቱን ይግለጽልሽ” ብሎ በእጁ ይባርክ።
 
 
 ይቆየን !
 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር