በዓለ ግዝረት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

በዓለ ግዝረት

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅድመ ዓለም በህሊና ያሰበውን፤ ድኅረ ዓለም በነቢያት ያናገረውን ለመፈጸም ሰው ሆነ፣ ሥጋ ለበሰ፤ ሕግ ጠባያዊን ሕግ መጽሐፋዊን እየፈጸመ በጥቂቱ አደገ። ሕግ ጠባያዊ፤ አበ፣ እመ ማለት፣ ለዘመድ መታዘዝ፣ በየጥቂቱ ማደግ ነው። “ወልህቀ በበኅቅ እንዘይትኤዘዝ ለአዝማዲሁ ወለይእቲ እሙ” እንዲል። ሕግ መጽሐፋዊ በስምንት ቀን ቤተ ግዝረት በአርባ ቀን ዕጉለ ርግብ ዘውገ ማዕነቅ ይዞ ቤተ መቅደስ መግባት የመሳሰሉት ናቸው፤ በማለት የመጻሕፍተ ሐዲስ ኪዳን ሊቃውንት በሐዲስ ኪዳን ትርጓሜ መግቢያ ላይ ያመሰጥራሉ፣ ያስተምራሉ።

ቅዱስ ሉቃስ በጻፈው የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ወንጌል ምዕራፍ 1 ቁጥር 59 ላይ ዘግቦልን እንደምናገኘው፤ በዘመነ ብሉይ ወንድ ልጅ በተወለደ በስምንተኛው ቀን ሲገረዝ ስም ይወጣለት ነበር።በመሆኑም ግዝረት የሥጋ ሸለፈት መቆረጥን ያመለክታል።

የግዝረት ሥርዓት ዝም ብሎ የመጣ ሳይሆን እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠው የቃል ኪዳኑ ምልክት ነው። ዘፍ17 ፤ 7-14 በሙሴ የመሪነት ዘመንም ለእስራኤል ህዝብ ምልክትና መለያ ነበር።ዘፀ 12፤43 ፈሪሳውያን ግን ከአብርሃም የመጣ መሆኑን ሳይረዱ በሙሴ እንደተሰጠ ሕጋዊና ሕዝባዊ ምልክት አድርገው ያምኑ ነበር።የሐዋ 15፤1-5 ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን፤ መጀመሪያ ራሱ የሰጠው ለአብርሃም እንደነበርና መንፈሳዊ ምልክትም እንደሆነ አስረድቷቸው ነበር።ዮኀ 7፤22።

የሚከተሉት ሦስት ነጥቦች የግዝረት ዋና ዋና ዓላማዎች ናቸው።

  1. እግዚአብሔር የተገረዘውን ሰው ለራሱ መርጧልና አምላኩ ነው፤ ዘፍ 17፤8
  2. የተገረዙት የእግዚአብሔር ህዝቦች ናቸውና ክፋትንም ከህይወታቸው ማስወገድ አለባቸው፤ ዘጸ 10፤16
  3. እግዚአብሔር በእምነት ስለተቀበላቸው የጽድቃቸው መሠረት ነው፤ ሮሜ 4፤11

ሆኖም በሐዲስ ኪዳን ሥርዓት ሣይሆን፤ የሚያድነው የእግዚአብሔር ህግ መሆኑን ቅዱስ ጳውሎስ ያብራራል።ሮሜ 2፤25 ዋናው ነገር የሥጋ ሸለፈት መገረዝ ሳይሆን የልብ መለወጥና በእግዚአብሔር ማመን ሕጉንም መፈጸም ነው፣ ሲል ቅዱስ ጳውሎስ ምዕመናኑን በመንፈስ የተገረዙ መሆናቸውንም ጨምሮ አብራርቷል።ፊሊጵ 3፤30 በተለይም ህዝብና አህዛብ ማለትም ትንቢት የተነገረላቸው፣ ተስፋ የተነገራቸው እስራኤላውያን እና ከአህዛብ ወገን የመጡት ሁለቱም የክርስትና አማኞች በግዝረት ምክንያት ያስነሱትን አለመግባባት አስመልክቶ በጻፈው መልእክቱ በሐዲስ ኪዳን ዘመን ጥምቀት በግዝረት ፋንታ መተካቱን ያስረዳል።ቆላ 2፤11 ግዝረትም አሁን አይጠቅምም ይለናል። ገላ 5፤6።

ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግዝረት ስንመለስ ደግሞ፤ በመግቢያው እንደተገለጸው ኦሪትና ነቢያትን ልፈጽም እንጂ ልሽራቸው አልመጣሁም እንዳለ፤ ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና እርሱ ራሱ ሥርዓቱን ለመፈጸም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ በስምንተኛው ቀን እናቱ ወደ ቤተ መቅደስ ወስዳው ሊገረዝ በታሰበ ጊዜ በፍጡራን እጅ አልተገረዘም። ምላጩ በገራዡ እጅ እንዳለ ውኃ ሆኖ ተገኝቷል (መጽሐፈ ስንክሳር ጥር ስድስት)።ይህም በመለኮታዊ ኃይሉ ነው። እርሱም በግብር መንፈስ ቅዱስ ተገርዞ ተገኝቷል።ይህንንም ያደረገው ሰውን ንቆ ስርዓቱንም ጠልቶ ሳይሆን ደመ መለኮቱ ያለ ዕለተ ዓርብ የማይፈስ ስለሆነ እርሱ ባወቀ ይህን አደረገ ስሙንም አስቀድሞ በመልአኩ እንደተነገረ ኢየሱስ አሉት። ሉቃ 2፤21

በዚህም ምክንያት ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የግዝረት በዓል በየዓመቱ ጥር 6 ቀን ታከብራለች (መጽሐፈ ስንክሳር ጥር ስድስት)። ስታከብርም በግዝረቱ እለት የተፈጸሙትን ተአምራት በማስተማርና በማሳወቅ ነው።

ለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ምስጋና  ይሁን! አሜን!

ርእሰ ደብር ብርሃኑ አካል