ቤተ መቅደስ ገባች

 

በቀናችው መንገድ  በሃይማኖት ጸንተው፣

በቅዱስ ጋብቻ ትእዛዙን አክብረው፣

ምግባር ከሃይማኖት አሰተባብረው  ይዘው፤

ጸሎት ያልተለየው ቅዱስ ሕይወታቸው፣

ኢያቄም ወሐና ልጅ ወልዶ ለመሳም ቢፈቅድም ልባቸው፣

ሳይወልዱ ሳይከብዱ ገፋ ዘመናቸው።

ጸሎታቸው ቢደርስ   ልጅን ቢሰጣቸው፣

ብጽዓት ነውና ከአምላክ ውላቸው

የአምላክ አያት ሆነው ድንግልን ሰጣቸው፡፡

ሐናና ኢያቄም  ከሁሉም ልቀዋል፣

ፈጣሪን የምትወልድ ድንግልን ወልደዋል።

ጸሎት ያልተለየው ቅዱስ ሕይወታቸው፣

የፈጣሪን እናት መውለድ አስቻላቸው።

የሐና የኢያቄም የከበረች ፍሬ፣

ምስጋና እየሰማች ውዳሴ ዝማሬ፣

በቤተ መቅደስ ውስጥ ልትኖር አገልግላ፣

ገባች ቤተ መቅደስ ሦስት ዓመት ስትሞላ።

ሐና ሰጥታት ስትሄድ አድርሳት ከመቅደስ፣

ድንግል ወደ እናቷ ስትሄድ ስትመለስ፣

ዝቅ አለ ፋኑኤል ከሰማይ ወረደ፣

በክንፎቹ ጋርዶ መግቧት ዐረገ።

የሦስት ዓመት ሕፃን ትንሽ ብላቴና፣

የበኩር ልጃቸው የኢያቄም የሐና፡፡

በክንፎቹ ጋርዶ መልአክ የመገባት፣

ቤተ መቅደስ ገባች የአማኑኤል እናት።

ሰማዮችን ቀደህ ምነው ብትወርድ ያለው፣

የኢሣይያስ ስብከት ፍጻሜው ደርሶ ነው።

አምላክን ለመውለድ ቀድማ የታሰበች፣

አሥራ-ሁለት ዓመት ቤተ መቅደስ ኖረች።

ኢያቄም ወሐና እናትና አባትሽ፣

ኅልም አይተው ነበረ ድንግል መጸነስሽ።

ተአምሩ ብዙ ነው እም አምላክ ልደትሽ፣

ቤተ መቅደስ ሆነ ድንግል ሆይ ዕድገትሽ።

ዝናብ የታየብሽ ትንሿ ደመና፣

አንቺ መሶበ ወርቅ ውስጥሽ ያለ መና።

«እንደ ልቤ» ብሎ አምላክ ስም የሰጠው፣

ከእረኝነት መርጦ ንጉሥ ያደረገው፣

በጸጋ ተመልተሽ ቢመለከት ከብረሽ፣

በግርማ በሞገስ ወርቅ ተጎናጽፈሽ፣

በሰማይ በክብር በቀኝ በኩል ቢያይሽ፡

ወትቀውም ንግሥት ብሎ ተቀኘልሽ።

የሁላችን_ተስፋ_የአዳም_የስብከት ቃል፣

የነቢያት ምሥጢር የሲና ሐመልማል፣

የሕዝቅኤል ራእይ የነቢያት ትንቢት፡

ቅኔው ለሰሎሞን መዝሙሩ ለዳዊት።

ተሰምቶ አይጠገብ ውዳሴሽ መብዛቱ፣

ለአባ ሕርያቆስ አንቺ ነሽ ድርሰቱ።

እናታችን ማርያም ጥዑመ ስም ያለሽ፣

ጥዑመ ስም ያለው ክርስቶስን ወልደሽ፣

ዓለም ይባረካል ይኸው እስከ ዛሬ፣

መድኃኒት ነውና ከአንቺ የወጣው ፍሬ።

የነደደው እሳት በሲና ሐመልማል፣

ምሳሌ ለድንግል ምሳሌ ነው ለቃል።

ያንን ነበር ያየው ሙሴ በድንቁ ቀን፣

መለኮት ማደሩን በድንግል ማኅፀን።

አባ ሕርያቆስ ውዳሴሽ በዝቶለት፣

የምስጋናሽ ነገር ምሥጢር ተገልጦለት፣

የክብርሽን ነገር በአድናቆት በማየት፣

ይመሰክር ጀመር በጣፈጠ አንደበት።

እግሩ ከምድር ሳይለቅ ሐሳብ አመጠቀው፣

በደመና ጭኖ የኋሊት ወሰደው።

ያሬድ በዝማሬው ንዑድ ክቡር ያለሽ፣

ድንግል እናታችን የገነት ቁልፍ ነሽ።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር።

አብርሃም_ሰሎሞን።