ዜና

በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል 22ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተካሄደ

በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል 22ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተካሄደ።
ከግንቦት 14 እስከ 16, 2012 ዓ/ም “በእናንተ ዘንድ ሁሉ በፍቅር ይሁን” 1ኛ ቆሮ 16፡14 በሚል መሪ ቃል ሲካሄድ የሰነበተው በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል 22ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በሰላም ተጠናቀቀ፡፡ ጠቅላላ ጉባኤዉ በዓለም አቀፉ ወረርሽኝ ምክንያት በርቀት ከመደረጉ በቀር በተሳካ ሁኔታ ተፈጽሟል። በጉባኤው ላይ ከ650 በላይ አባላት በርቀት በ’Zoom’ የተሳተፉ ሲሆን ጉባኤዉ በጊዜ አጠቃቀምም ሆነ በጉባኤው አባላት ሱታፌ ገጽ ለገጽ ከሚደረገው የጎደለ ሳይኖር የተፈጸመ ነበር።
የጉባኤው መክፈቻ ዓርብ ማታ በጸሎት የተጀመረ ሲሆን ዋናው ጉባኤ ቅዳሜ ጠዋት በሰሜን አሜሪካ ባሉ 3 ሊቃነ ጳጳሳት ማለትም ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኮሎራዶና አካባቢው ሐገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ የሰሜን ካሊፎርኒያ፣ ኔቫዳና አሪዞና ሐገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የዋሽንግተን፣ ኦሪገን፣ አይዳሆና አካባቢው ሐገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በጸሎተ ወንጌል ተከፍቷል። በእለቱ መልአከ አርያም ቀሲስ ብርሃኑ ጎበና የጠቅላላ ጉባኤውን መሪ ቃል “በእናንተ ዘንድ ሁሉ በፍቅር ይሁን” መነሻ በማድረግ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡ ቀጥሎም የአሜሪካ ማዕከል መልዕክት በማዕከሉ ሰብሳቢ በዲ/ን ተገኔ ተክሉ ቀርቦ በእለቱ የተገኙት ብፁዓን አባቶች መመሪያና ቃለ ምእዳን ሰጥተዋል። በመቀጠል 2011/2012 ዓ/ም እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ከማኅበሩ ስልታዊ እቅድ አንጻር በእቅድ ዝግጅት ክትትልና ጥናት ዋና ክፍል ኃላፊ፣ የሂሳብ ክፍል ሪፖርት በሂሳብና ገቢ አሰባሳቢ ዋና ክፍል ኃላፊ እንዲሁም የኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ሪፖርት በአገልግሎቱ ኃላፊ ቀርቧል፡፡

በዚሁ እለት በዋናው ማዕከል ተወካይና የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ አቶ ታምሩ ለጋ የዋናው ማዕከል መልእክት የቀረበ ሲሆን ተሳታፊ አባላት በሪፖርቶቹ ላይ ያላቸውን ጥያቄዎችና አስተያየቶች በጽሑፍ ከተሰበስቡ በኋላ በማእከሉ ስራ አስፈጻሚ አባላት ምላሽ ተሰጥቷል። ከቀረቡት አስተያየቶች ውስጥ ስምምነት የተደረሰባቸው በእቅድ ውስጥ እንዲካተቱ አቅጣጫ በመስጠት ጠቅላላ ጉባኤው የቀረቡትን እቅዶች አጽድቋል::

የእሁድ መርሐግብር በአባቶች ጸሎት ከተከፈተ በኋላ ቅዳሜ ዕለት በነበረው ጉባኤ በሪፖርቶቹ ላይ ከዋናው ማዕከል ተወካይ ግብረ መልስና አስተያየቶች የተሰጠ ሲሆን ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ሁኔታና የማኅበሩን አገልግሎት በተመለከተ በዋናው ማዕከል ተወካይ አጭር ገለጻ ተደርጓል። ከዚያም ማዕከሉን ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት የሚመሩ የሥራ አስፈጻሚ አባላትን በማኅበሩ ደንብና አሠራር መሰረት በዕጣ እንዲመረጡ ተደርጓል:: በእለቱ የ2013 ዓ.ም እቅድ በዝርዝር ቀርቦ የጉባኤው ተሳታፊዎች በምድብ ተከፋፍለው ጥልቅ ውይይት ካደረጉበት በኋላ ሁሉም ቡድኖች ያነሷቸው በእቅድ ሊካተቱ የሚገባቸው ሃሳቦች እና በቀረበው እቅድ ላይ የተሰጡ አስተያየቶች ተካተው እቅዱ ጸድቋል:: ከአባቶችና ከጉባኤው ተሳታፊዎች አስተያየቶች ከተሰጡ በኋላ ባለፉት ሁለት ዓመታት በማዕከሉ ሥራ አስፈጻሚነት ላገለገሉና አዲስ ለተመረጡ ሥራ አስፈጻሚ አባላት ጸሎት ተደርጎል:: በመጨረሻም የ22ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ዝግጅት ኮሚቴ አጭር የሥራ ሪፖርት ያቀረበ ሲሆን የአሜሪካ ማእከል የሚቀጥለው 23ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በዚህ ዓመት ሊካሄድ ታስቦ በነበረበት በዴንቨር ኮሎራዶ እንደሚካሄድ ተገልጿል። በሁለቱም ቀናት በጉባኤው የተጋበዙ ማኅበራት ማኅበረ ባለወልድ፣ የሰሜን አሜሪካ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት፣ UOTY፣ YOTC እና በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓና የካናዳ ማዕከላት ተወካዮች መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን የአሜሪካ ማዕከል ከማኅበራቱ ጋር በመመካከር እየሰራቸው ያሉ ሥራዎችን የበለጠ በማጠናከር ለአንዲት ቤተክርስቲያን አገልግሎት መጠናከር በተቀናጀ መልኩ መሥራት እንደሚያስፈልግ ተገልጿል። ጉባኤው በጸሎት ከተዘጋ በኋላ አባላቱ ሲዘምሩ ያመሹ ሲሆን ከ200 በላይ አባላትም ሌሊቱን ሙሉ ሲወያዮ አድረው ለ24 ሰዓት ጉባኤ ላይ መቆየታቸውን ሲገነዘቡ “ትናንት ያየናትን ፀሐይ እነሆ ደግመን አየናት” ሲሉ ኃይልና ብርታት የሰጣቸውን አምላክ አመስግነዋል::

ከዋናው ጉባኤ ጎን ለጎን የአዳጊዎችና ወጣቶች 2ኛው ጠቅላላ ጉባኤ በልዩ ሁኔታ ተዘጋጅቶ ከ200 በላይ የአባላት ልጆችና የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን በመርሐ ግብሩም ላይ ትምህርት፣ መዝሙር፣ ሥነ ጽሁፍ፣ የፓናል ዉይይትና ጥያቄና መልስ ቅዳሜና እሁድ በእያንዳንዱ ቀን ለ2 ሰዓታት ቀርቧል። ይህ የአዳጊዎችና ወጣቶች መርሐግብር ትኩረት ተሰጥቶት ራሳቸው ልጆቹ ባለቤት ሆነው የሚያዘጋጁበት መንገድ በቀጣይም እንዲቀጥል ማሳሰቢያ ተሰጥቷል፡፡
የከርሞ ሰው ይበለን::

ማኅበረ ቅዱሳን በአትላንታ አስረኛውን የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማዕከል ከፈተ!

 ቀን ነሐሴ 14 ቀን 2011

ማኅበረ ቅዱሳን  በአትላንታ አስረኛውን የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማዕከል ከፈተ!

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን  በሰሜን አሜሪካ ማዕከል የአትላንታ ንዑስ ማዕከል አስረኛውን የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማዕከል ከፈተ፡፡

 

ከማዕከሉ የተተኪ ትውልድና ግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ክፍል ሪፖርት መረዳት እንደተቻለው ፤ ማዕከሉ ከ፸፭ (ሰባ አምስት) በላይ ተማሪዎችን ተቀብሎ  ለማስተማር  ዝግጅቱን አጠናቆ ሐምሌ ፳፯ ቀን ፳፻፲፩  ዓ.ም ተማሪዎችና ቤተሰቦቻቸው በተገኙበት  አገልግሎቱን መስጠት መጀመሩ ታውቋል።

 

ማኅበሩ በሰሜን አሜሪካ በሰባት የአሜሪካ ግዛቶች ማለትም በሲያትል ሦስት፣ በቨርጅኒያ፣ በዋሽንግተን ዲሲ፣ በዳላስ፣ በቦስተን፣ በኖርዝ ካሮላይናና  በኢንዲያና የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማዕከላትን ከፍቶ ከ ፭፻፶ (አምስት መቶ ሐምሳ) በላይ የሆኑ ልጆችንና አዳጊ ወጣቶችን ትምህርተ ሃይማኖት፣ አማርኛ ቋንቋ፣ ታሪክ፣ የአብነት ትምህርትና የመሳሰሉ ትምህርቶችን ሲሰጥ የቆየ ሲሆን ፤ አገልግሎቱን በማስፋት የአትላንታው የትምህርት ማዕከል መከፈት ማኅበሩ በሰሜን አሜሪካ  ያሉትን የትምህርት ማዕከላቱን  ቁጥር ከዘጠኝ ወደ አስር ከፍ ያደርገዋል።

 

በተያያዘ ዜና የአትላንታ ንዑስ ማዕከል የተተኪ ትዉልድና ግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያ ክፍል ስምንት  የ፲፪ኛ (አስራ ሁለተኛ) ክፍል ተማሪዎችን በቅድመ ግቢ ጉባኤ መርኃ ግብር ለአራት ወራት  ኮርስ ሰጥቷል፡፡ ኮርሶቹም ፭ቱ አዕማደ ምስጢራት፣ ፯ቱ ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን፣ ነገረ ክርስቶስ፣ ነገረ ማርያም፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክና  ነገረ ቅዱሳን ትምህርቶችን በመካነ ሕይወት አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ቤተክርስቲያን በየሳምንቱ ቅዳሜ  ለሁለት ሰዓት ተኩል አስተምሮ ፤ ሰኔ ፱  ቀን ፳፻፲፩  ዓ.ም (June 15, 2019)  በአትላንታ ዳግማዊ ቁልቢ ደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ወተክለሃይማኖት በተክርስቲያን አስመርቋል።

 

 

በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል 21ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተካሄደ

ከዓርብ ግንቦት 16 ቀን 2011 ዓ/ም እስከ ግንቦት 19 2011 ዓ/ም በኔቫዳ ግዛት ላስቬጋስ ከተማ “በሰላም ማሠሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ” ኤፌ 4፡3 በሚል ኃይለ ቃል ሲካሄድ የሰነበተው በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል 21ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በሰላም ተጠናቀቀ፡፡” .. ”

በአሜሪካ ማእከል ሥር ካሉት 12 ንኡሳን ማእከላትና 10 ግንኙነት ጣቢያዎች የመጡ የማኅበሩ አባላትና የአባላት ቤተሰቦች፣ ተጋባዥ እንግዶች፣ በላስ ቬጋስ ከተማ ያሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት የደብር አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ዲያቆናት ባጠቃላይ 372 ጉባኤተኞች የተሳተፉበት ይህ ጉባኤ ዓርብ ግንቦት 16 ቀን በሐመረ ኖህ ቅድስት ኪዳነምሕረት ወቅዱስ ሚካኤል ካቴድራል በጸሎት ተጀምሯል፡፡

በማግስቱ ቅዳሜ ግንቦት 17 ቀን 2011 ዓ/ም መርሐግብሩ በጸሎተ ወንጌል ከተከፈተ በኋላ በላስቬጋስ ንኡስ ማእከል ሕጻናት እና የአሜሪካ ማእከል መዘምራን የኅብረት መዝሙር አቅርበው መምህር ሙሉጌታ ኃይለማርያም የጠቅላላ ጉባኤውን መሪ ቃል “በሰላም ማሠሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ” መነሻ አድርገው ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡ ቀጥሎም በተከታታይ የአሜሪካ ማእከል መልእክት በማእከሉ ሰብሳቢ፣ የ2010/2011እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ከማኅበሩ ስልታዊ እቅድ አንጻር በእቅድ ዝግጅት ክትትልና ጥናት ዋና ክፍል ኃላፊ፣ የሂሳብ ክፍል ሪፖርት በሂሳብና ገቢ አሰባሳቢ ዋና ክፍል ኃላፊ፣ እንዲሁም የኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ሪፖርት በአገልግሎቱ ምክትል ኃላፊ ቀርቦ ውይይት ተካሂዶባቸዋል፡፡

ቅዳሜ ጠዋት መርሐግብር ፍጻሜ ላይ በሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ብጹዕ አቡነ ቴዎፍሎስ ፈቃድ በማኅበረ ቅዱሳን 21ኛው ጠቅላላ ጉባኤ የሰሜን ካሊፎኒያ ኔቫዳ እና አሪዞና ሀገረ ስብከት ተወካይ መጋቤ ምሥጢር አባ ቴዎድሮስ ዘውዱ ባስተላለፉት መልእክት በኅብረትና በአንድነት ማገልገል ያለውን ጠቀሜታ፡ አበክረው አስረድተዋል። በተጨማሪም ፡ ለሀገርም ፡ ለቤተ ክርስቲያንም ትልቅ ለውጥ የሚያመጣ ሥራ መሥራት የሚቻለው መስመር ባለው ተቋማዊ አሠራር ይዞ በመሥራት ስለሆነ የማኅበሩ አባላት የተቋሙን አገልግሎት መጠበቅ እንደሚገባቸው ፤ በአገልግሎት ወቅት በሚመጡ የተለያዩ ፈተናዎች ተስፋ ሳይቆርጡ በአገልግሎት ጸንተው መንፈሳዊ ሕይወታቸው ላይ ትኩረት ሰጥተው ሊሠሩ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

ጉባኤው በቅዳሜ ከሰዓት በኋላ በተያዘለት መርሐግብር መሠረት በቀረቡት ሪፖርቶች ላይ ሰፋ ያለ ተጨማሪ ውይይት ያደረገ ሲሆን “ወቅታዊ ሀገራዊ ለውጡን ከአገልግሎት አንጻር መረዳት” እና “የአኅጉረ ስብከት አገልግሎትን ለማጠናከር ያሉ በጎ እድሎችና ተግዳሮቶች” በሚሉ ሁለት ርእሰ ጉዳዮች ላይ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል።

ቀጥሎም በአቡነ ጎርጎርዮስ ካልእ የተተኪ ትውልድ ክፍል አስተባባሪነት በየኔታ ወልደገብርኤል ይታይህ የተዘጋጀው “በግእዝ ንባብ የውዳሴ ማርያም ጸሎት መማሪያ” ሲዲ ተመርቆ ለአገልግሎት እንዲተዋወቅ ተደርጓል፡፡ በዚሁም ወቅት በማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የተዘጋጀው የሕጻናትና አዳጊዎች ማስተማሪያ ሥርዓተ ትምህርት የመምህሩ መምሪያ አምስት መጻሕፍት በአሜሪካ ማእከል የተተኪ ትውልድ ክፍል በኩል ታትመው በአሜሪካ ላሉ አብያተ ክርስቲያናት በሙሉ በነጻ ለሥርጭት መዘጋጀታቸው ተገልጿል፡፡
ከዚሁ መርሐግብር ተከትሎ በዝክረ አበው ወዕም መርሀ ግብር “የሰሙነ ሕማማት እንግዳ” በሚል ርዕስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለ32 ዓመታት በከፍተኛ ተጋድሎና ትጋት ስላገለገሉት ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ/ ኃይለመስቀል/ የሚዘክር፡ አርያነታቸውንም የሚያስተምር ዝግጅት በበኩረ ትጉሃን ቀሲስ ኤርምያስ ቀርቧል፡፡

በእለቱ መርሐግብር ላይ የቤተ ማኅበረ ቅዱሳን ኮሚቴ ሰብሳቢ ስለ ቤተ ማኅበረ ቅዱሳን የኮሚቴውን የሥራ ሪፖርት አቅርበዋል፡፡ በሪፖርታቸውም የአሜሪካ ማእከል የራሱ የሆነ የጽሕፈት ቤትና የሥራ ማስኬጃ ቦታ እንዲኖረው ለማድረግ የተደረገው ከፍተኛ ጥረትና ድካም ፍሬ ማፍራቱንና የመጨረሻ ደረጃ ላይ መድረሱን ገልጸው ጉባኤተኛውም የግዥ ሂደቱን ለማቀላጠፍና ከብድር እዳ ነጻ የሆነ ሕንጻ ለመግዛት የሚያስፈልገውን ቀሪ ገንዘብ ለማዋጣትና አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ቃል ገብቷል፡፡
በመጨረሻም በአባቶች ጸሎት የቅዳሜው መርሐግብር ተጠናቋል፡፡

እሑድ ጠዋት ለጉባኤው የመጡ ካህናት አባቶች እና አባላት በ ቬጋስ በሚገኙ የኢ/ኦ/ተ አብያተክርስቲያናት በተመደቡበት አጥቢያ በመገኘት ቀድሰዋል፣ አስቀድሰዋል። እሑድ ከሰዓት በኋላ በቀጠለው መርሐግብር የ2011/2012 ዓ.ም ዓመታዊ እቅድ የትኩረት አቅጣጫዎችና በጀት ለጉባኤው የቀረበ ሲሆን ጉባኤው በሶስት ምድብ በመሆን በእቅዶቹ ላይ ውይይት ተካሂዶባቸውል፡፡ እንዲሁም ለቀረቡ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡
በእለቱ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ በአሜሪካ” እንደዚሁም “ለውጥ የሚያመጣ አገልግሎት” የሚሉ ዝግጅቶች ቀርበዋል። ለጉባኤው ከተጋበዙት ባለድርሻ አካላትም የበዓለወልድ ማኅበር፣ የሰ/ት/ቤቶች አንድነት (NASSU)፣ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ወጣቶች ህብረት(UOTY)፣ እና የወጣት የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ክርስቲያኖች (YOTC ) መልእክት በተወካዮቻቸው ለጉባኤው ተነቧል።በጉባኤው ማጠቃለያ ላይ ካህናት አባቶች ተጋባዥ ወንድሞችና እህቶች በመንፈሳዊ ሕይወታችን ጠንክረን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እንዴት ልናገልገል እንደሚገባ ተሞክሯቸውን አካፍለዋል፡፡

በመጨረሻም የ21ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ዝግጅት ኮሚቴ የሥራ ሪፖርትና ክንውን ሂደት ቀርቦ ከአባቶች ምስጋናና ጸሎት ተደርጎላቸዋል፡፡ በሪፖርቱ እንደተጠቀሰው ከዋናው ጉባኤ ጎን ለጎን የሕጻናትና አዳጊዎች መርሐግብር በልዩ ሁኔታ ተዘጋጅቶ 95 ልጆች እንደተሳተፉበትና በሦስት ደረጃ ተከፋፍለው እድሜያቸውን የሚመጥን ትምህርትና ዝግጅት እንደተከታተሉ ተገልጿል፡፡ ይህ የሕጻናትና አዳጊዎች መርሐግብር ትኩረት ተሰጥቶት ራሳቸው ልጆቹ ባለቤት ሆነው የሚያዘጋጁበት መንገድ በቀጣይም እንዲቀጥል ማሳሰቢያ ተሰጥቷል፡፡ የአሜሪካ ማእከል የሚቀጥለው 22ኛ ጠቅላላ ጉባኤ የሚካሄደው በዴንቨር ኮሎራዶ መሆኑ በዚሁ ወቅት የተገለጸ ሲሆን መርሐግብሩ በዝማሬና በአባቶች ጸሎት እሑድ ሌሊት ተፈጽሟል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል አዘጋጅነት የባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር ጉባኤ ተደረገ

የኢ/ኦ/ተ ቤ/ክርስቲያንን አገልግሎት ለሕፃናት ፣ አዳጊዎችና ወጣቶች እንዲሁም ለተጠመቁና ለሚጠመቁ የውጭ አገር ዜጎች ለማድረስና ለማስፋፋት ከሚያገለግሉ ባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር ጉባኤ ተደረገ።

 

በሁሉም የባለድርሻ አካላት በተናጠል የሚሠሩ ሥራዎችን ለማጠናከርና በይበልጥም በቅንጅት ሊሠሩ የሚገባቸውን ሥራዎች በመለየትና አቅምንና ሀብትን በተጠና መልኩ በማቀናጀት የሚፈለገውን ለውጥ በማምጣት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በውጭ ሀገር የጀመረችውን ሐዋርያዊ ተልዕኮ ማፋጠን ይቻል ዘንድ ይህን የመጀመርያ የምክክር መድረክ በአሜሪካ ማዕከል አስተባባሪነት በየካቲት 9 2011 ዓ ም በዲሲ ርዕሰ አድባራት ደብረ ሰላም ቅድስት ማርያም የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ መዘጋጀቱ ተገልጿል። 

 

በመርሃ ግብሩም የዲሲና አከባቢዋ ሃገረ ስብከት ዋና ጸሐፊ መልአከ አርያም ቀሲስ ብርሃኑ ጎበና፣ ከሊቃውንተ ቤተክርስቲያን መልአከ ሰላም ቀሲስ ዳኛቸው ካሳሁን፣ እንዲሁም ሥራው እየተሳተፉ ያሉ የካህናት ተወካዮች፣ የማኅበረ በዓለወልድ፣ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ወጣቶች ሕብረት (UOTY)፣ የወጣት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስቲያኖች (YOTC) እና  የሰሜን አሜሪካ ሰ/ት/ቤቶች ህብረት (NASSU) አመራር አካላት፣ የርዕሰ አድባራት ደብረ ሰላም ቅድስት ማርያም የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ተወካዮች እና በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል አመራር አካላት እና አባላት ተሳትፈውበታል።e

በጉባኤውም በቀሲስ ሰይፈሥላሴ ጥናታዊ ጽሁፍ ቀርቦ ውይይት የተደረገበት ሲሆን ሊቃውንተ ቤተክርስቲያንና ካህናት እንዲሁም የጉባኤው ተሳታፊዎች የአገልግሎት ማኅበራት የአገልግሎት ልምዳቸውን ለጉባኤው አካፍለዋል። በመቀጠልም ህጻናትን፣ አዳጊዎችንና ወጣቶችን እንዲሁም የውጭ አገር ዜጎችን ትምህርተ ሃይማኖት ለማስተማርና ለድኅነት ለማብቃት የሚደረገው አገልግሎት ካለው የምእመናን ቁጥር ብዛት፣ የባህል፣ የቋንቋ ልዩነትና ከባቢያዊ ተጽእኖ አንጻር በቂ እንዳልሆነና ብዙ በተጠናና በተቀናጀ መልኩ መሥራት እንደሚገባ በተሳታፊዎች ተጠቅሷል።

በመቀጠልም በአሜሪካ ማዕከል አመራር አካላት በማኅበረ ቅዱሳን 4ኛው ዙር ስልታዊ ዕቅድ መሠረት ለቤተክርስቲያን ተልዕኮ ውጤታማነት የባለድርሻ አካላት ትብብርና አቅም ማቀናጀት ወሳኝና አስፈላጊ በመሆኑ ሁሉም የባለድርሻ አካላት በጥናታዊ ጽሑፉና በውይይቱ የተጠቀሱትን የአገልግሎት ኃላፊነት በመውሰድ በታቀደና በሚለካ መልኩ መሥራት እንደሚገባ በአጽንኦት ተገልጿል።

 በመጨረሻም የዲሲና አከባቢዋ ሃገረ ስብከት ዋና ጸሃፊ መልአከ አርያም ቀሲስ ብርሃኑ ጎበና  በሃገረ ስብከቱ ባሉ መዋቅሮች ይህንን አገልግሎት በተጠናከረ መልኩ ለመደገፍና ለማስቀጠል ዝግጁነት እንዳለና ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት ማበርከት እንደሚገባ አሳስበዋል።

ለዚሁ የምክክር ጉባኤ ዝግጅት መሳካት የድርሻቸውን ለተወጡ ለዲሲ ርዕሰ አድባራት ደብረ ሰላም ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስተዳደርና ምዕመናን፣ ለዲሲና ቨርጂኒያ ንዑሳን ማዕከላት አባላትና ዝግጅቱን በበጎ ፈቃድ በድምጽ ወምስል በመቅረጽ ሙያዊ ድጋፍ ላበረከተው አቶ ሲሳይ አሸናፊ በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል መንፈሳዊ ምስጋና አቅርቧል።

 

በማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማዕከል አስተባባሪነት በተያዘው በጀት ዓመት ከተለያዩ አጥቢያዎች ለተወከሉ 59 የቤተክርስቲያን አገልጋዮች በተለያዩ 3 ቦታዎች በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተተኪ መምህራን ሥልጠና ተሰጠ።

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማዕከል ትምህርት፣ ሐዋርያዊ ተልዕኮና ምክር አገልግሎት ዋና ክፍል በተያዘው ዓመት በዲሲ፣ በሲያትልና በዳላስ ከአራት ንዑሳን ማዕከላት፣ ሦስት አጥቢያዎችና ሦስት ሰ/ት/ቤቶች ጋር በመተባበር በእንግሊዝኛ ቋንቋ ትምህርተ ወንጌልን ማስተማር የሚችሉ 59 ሰባኪያንን አሠለጠነ፡፡ 

በማዕከሉ የትምህርት፣ ሐዋርያዊ ተልዕኮና ምክር አገልግሎት ዋና ክፍል በተዘጋጀው በዚህ ሥልጠና ከተለያዩ አጥቢያዎች የተወከሉ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ሙሉ ለሙሉ ተሳትፈዋል፡፡

 

በዋና ክፍሉ ሪፖርት እንደተገለጸው የሥልጠናው ዓላማ ሠልጣኞቹ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ወንጌልን ሊያዳርሱ የሚችሉበትን ዕውቀትና ክህሎት እንዲያዳብሩ ለማገዝ ሲኾን ትምህርተ ሃይማኖት (ዶግማ)፣ ሥርዓተ ቤተክርስቲያን፣ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን፣ የቤተክርስቲያን ታሪክና የስብከት ዘዴ በሥልጠናው የተካተቱ የትምህርት ዓይነቶች ናቸው፡፡ ሥልጠናዎቹ የተሰጡትም ከየካቲት 8 እስከ 10 2011 ዓ.ም በዲሲና አከባቢው ሀገረ ስብከት ሥር በሚገኘው ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ካቴድራል፣ ከጥቅምት 30 እስከ ህዳር 2 ፣ 2011 ዓ.ም በሲያትል ደብረ ምህረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያንና ከጥቅምት 16 እስከ 18 2011 ዓ.ም ደግሞ በዳላስ ደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያን ነው፡፡ ሥልጠናውን በመስጠትም ቀሲስ ሰይፈ ሥላሴ ጎርደን ከካንሳስ ሲቲ፣ ቀሲስ ሱራፌል ወንድሙ ከሲያትል እንዲሁም ዲ/ን ዓለማየሁ ደስታ ከዳላስ ተሳትፈዋል፡፡

ሰልጣኞቹ በነበራቸው ቆይታ ከሥልጠናው ያገኙትን እውቀትና ልምድ በመጠቀምና የበለጠ በማስፋት ለቤተክርስቲያናቸው ሐዋርያዊ ተልዕኮ መፋጠን የበኩላቸውን እንደሚወጡ በመናገር በቀሰሙት የቤተክርስቲያን ትምህርት መደሰታቸውን ገልጸዋል፡፡

ልዩ ልዩ ተሳትፎ በማድረግ ለሥልጠናው መሳካት ድርሻቸውን ለተወጡ ለዳላስ ደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያን ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስተዳደርና ምዕመናን፣ ለሲያትል ደብረ ምህረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስተዳደርና ምዕመናን፣ ለዲሲ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ካቴደራል ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስተዳደርና ምዕመናን እንዲሁም ለደብሩ ፈለገ አበው ሰ/ት/ቤት፣ ለዲሲ ርዕሰ አድባራት ደብረ ሰላም ቅድስት ማርያም የፍቅር ኅብረት ሰ/ት/ቤት፣ ለሜሪላንድ ኆኅተ ምሥራቅ አምደ ሃይማኖት ሰ/ት/ቤት እንዲሁም ለዲሲና ቨርጂኒያ ንዑሳን ማዕከላት የማዕከሉ የትምህርት፣ ሐዋርያዊ ተልዕኮና ምክር አገልግሎት ዋና ክፍል በማኅበረ ቅዱሳን ስም መንፈሳዊ ምስጋና አቅርቧል፡፡

በእንግሊዝኛ ቋንቋ የሚሰጠው የተተኪ መምህራን ሥልጠና እንደሚቀጥልና ከዚህ በፊት ሥልጠናውን ለወሰዱ የማጠናከሪያ ስልጠና፣ ላልወሰዱ ደግሞ  ልዩ ልዩ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በመጠቀም ይህንኑ ሥልጠና እንዲወስዱ ለማድረግ ዝግጅት ላይ እንደሚገኝ የአሜሪካ ማዕከል የትምህርት፣ ሐዋርያዊ ተልዕኮና ምክር አገልግሎት ዋና ክፍል አስታውቋል፡፡

 

ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤው ስኬታማ እንደነበር ተገለጸ፡፡

ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ  ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤው ስኬታማ እንደነበር ተገለጸ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓና  የአሜሪካ ማዕከላት አስተባባሪነት ከጥቅምት ፲-፲፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም/October 20-21/2018  በሰሜን አሜሪካ  አትላንታ  ጆርጂያ የግዕዝ ሥነ ጽሑፍና የብራና ቅርሶች በኢትዮጵያ በሚል መሪ ቃል ሁለተኛው  ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ  ስኬታማ እንደነበር  የኮሚቴው  ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ተፈራ  ገለጹ፡፡

ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ተፈራ ጉባኤው  መጠናቀቁን  አስመልክተው ባደረጉት የማጠቃለያ ንግግር   በሁለቱ ቀናት ጉባኤ ከአውሮፓ፣ከኢትዮጵያ፣ ከአሜሪካ  የተለያዩ  ክፍለ ግዛቶች በመጡ ኢትዮጵያውያንና  የውጭ ተመራማሪዎች 3 ቁልፍ  ንግግሮችና 13 ጥናቶች ቀርበዋል፡፡ ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ፣ ፕ/ር  ስቲፍ  ዴልማተርና  ሊቀ ካህናት  ኃይለ ሥላሴ ዓለማየሁ  “ቁልፍ  ተናጋሪ“ በመሆን ጥናቶቻቸን  ያቀረቡ ሲሆን   የብራና መጻሕፍትና የግዕዝ ሥነ ጽሑፍን  መሰረት ያደረጉ የሃይማኖት፣የታሪክ፣የዜማ፣የቋንቋና ባሕል፣ የመድኃኒት፣ የትርጓሜ፣ የዘመናዊ ቴክኖሎጂ፣የብራና አዘገጃጀትን የተመለከቱ ጥናቶች በተመራማሪዎቹ  ቀርቦ ውይይት ተደረጓል፡፡

የጉባኤው ተሳታፊዎች፤ በእለቱ ጉባኤውን በጸሎት የከፈቱትና ቃለ ምዕዳን የሰጡት ብፁዕ አቡነ ሰላማ በሰሜን አሜሪካ የፍሎሪዳና  ኦሀዮ ሀገረ ስበከት ሊቀጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፣ የአትላንታ  ጆርጅያ  ከተማ  ምእመናን (የማኅበረ ቅዱሳን አባላት)፣ የደብር አለቆች፣ የውጭ ዜጎች (ጃማይካውንን ጨምሮ)  መሆናቸውን  ገልጸዋል፡፡ የጉባኤው ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት ዓለም አቀፍ  የጥናት ጉባኤው በመቅረቡ ደሰተኛ መሆናቸውን ገልጸው በጉባኤው ያልተሳተፉ ሰዎች ብዙ ምስጢር እንዳመለጣቸው ገልጸዋል፡፡

ጥቁር አሜሪካዊቷ  ዶ/ር ጌይ  ባይረን  ጥናታቸውን  ሲያቀርቡ  እንደገለጹት “ የኢትዮጰያ  ቤተክርስቲያን ባለውለታችን ናት::  የብራና መጻሕፍቱ በተለያየ ዓለም መገኘታቸው የቀደሙ አባቶች እውቀትና ተጋት ከፍተኛ እንደነበር ያስረዳል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ተሰፋችን ናት፡፡ ኢትዮጵያን አይቻለሁ፡፡  ደብረ ሊባኖስ ገዳምም ደርሻለሁ፡፡ የአብነት ተማሪዎች ሲማሩ  ተመልክተን ደስ ብሎናል፡፡  ባለፈው ሁለት ዓመታት የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ብራና መጽሐፍ አስመልሰናል፡፡ ወደፊትም  ከእናንተ ጋር ብዙ ለመስራት አሰባለሁ፡፡“  ብለዋል፡፡

ሊቀ ካህናት  ኃይለ ሥላሴ ዓለማየሁ በጉባኤው መዝጊያ ወቅት ሲገልጹ ”ዛሬ ተሰፋዬን አለመለማችሁት  አምላኬን አመሰግናለሁ ፡፡ ሁሉ እያላት ደሃ ለሆነችና ጠበቃ  ላጣች  ቤተክርስቲያን  ጠበቃ ሁኗት ፡፡ “ በማለት የጉባኤውን ተሳታፊዎች አደራ በማለት በጸሎት ዘግተዋል፡፡

ሦስተኛው  ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የጥናት ጉባኤ የትና መቼ እንደሚሆን ኮሚቴው የሚገለጽ ሲሆን በርካታ ተመራማሪዎች ሊሳተፉበት ይችላሉ ተብሎ ይገመታል፡፡

 

በኒውዮርክና ኒውጀርሲ የሚገኙ አብያተ ክርስትያናት የአንድነት ጉባኤ አካሄዱ

በኒውዮርክና ኒውጀርሲ የሚገኙ አብያተ ክርስትያናት የአንድነት ጉባኤ አካሄዱ

ታላላቅ ሊቃውንተ ቤተ ክርስትያን ፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ምዕመናን በተገኙበት በደመቀ ሁኔታ የሰላም እና የአንድነት ጉባኤ በሰሜን አሜሪካ ኒዋርክ ኒውጀርሲ ብስራተ ገብርኤል ቤተ ክርስትያን ጥቅምት ፫ ፳፻፲፩ ዓ.ም ተካሄደ። የኒውዮርክ ጽዮን ቅድስት ማርያም አስተዳዳሪ መልአከ ገነት ገዛኸኝ ፀሎተ ቅዳሴውን የመሩት ሲሆን ፣ የዕለቱ ትምህርተ ወንጌል “ምሕረትን እወዳለሁ’’ (ማቴ ፱፡፲፫) በሚል ርዕስ በመጋቤ ወንጌል ኤልያስ የብስራተ ገብርኤል ቤተ ክርስትያን ሰባኬ ወንጌል ተሰጥተዋል። በመቀጠል መልአከ ሰላም ዳኛቸው በእንግሊዝኛ ትምህርት የሰጡ ሲሆን ያለፈውን የመለያየት ዘመን ለቤተ ክርስትያን የጨለማ ጊዜ እንደነበረ አስታዉሰው ከዚህ በኋላ ግን ቤተ ክርስትያንን በአንድነት ማገልገል እንደሚገባ መልእክት አስተላልፈዋል። በዚህ ጉባኤ በ ኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ከሁለት የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተናጋሪ አብያተ ክርስትያናት የመጡ ምዕመናን ተገኝተዋል።በዓሉን በተመለከተ ከሁሉም አብያተ ክርስትያናት የተውጣጡ ህፃናት እና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች መዝሙር አቅርበዋል።

በመቀጠል የኒውዮርክ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስትያን አገልጋይ ርዕሰ መምህራን ብርሃኑ በዓሉን በተመለከተ የቅዱስ ያሬድ ወረቦችን አሰምተዋል። ምዕመናን በዕልልታ እና በጭብጨባ ከሊቃውንቱ እና ከመዘምራን ጋር አብሮ በመዘመር ለዚህ አንድነት ያበቃቸውን እግዚአብሔርን አመስግነዋል። ቅዳሴው፥ዝማሬው ልብን የሚመሰጥ ፣ መንፈስን የሚያድስ እና የሚያረጋጋ እጅግ በጣም ልዩ ነበር። ቀጥሎም የደስታ መግለጫ መልአከ ገነት ገዛኸኝ ያቀረቡ ሲሆን መለያየት ጥሩ ባይሆንም ቤተ ክርስትያን እንድትሰፋ ምክንያት ሁኗል ብለዋል። ከዚህ በኋላ ግን ቤተ ክርስትያንን በአንድነት በማገልገል እንደ መስቀል እና ጥምቀት ያሉ ዓበይት በዓላትን በጋራ ማክበር እንደሚገባ መክረዋል።ርዕሰ መምህራን ብርሃኑ ተመሳሳይ መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን መወድስ ቅኔ በግዕዝ እና በአማርኛ ቀርቧል። በተለይ የሴራክዮስ ገነተ ደናግል ቅድስት አርሴማ ወክርስቶስ ሠምራ ገዳም አስተዳዳሪ የሆኑት መልአከ ገነት ካሳሁን እንባ እየተናነቃቸው ያስተላለፉት መልእክት የብዙዎችን ልብ የነካ ነበር። ቤተ ክርስትያን  የማሕበረሰብ (Community) አገልግሎት ሳይሆን ምዕመናንን ቅዱስ ስጋውን ክቡር ደሙን ተቀብለው ወደ መንግስተ ሰማያት ለመግባት የሚዘጋጁባት ቤተ መቅደስ መሆን እንዳለባት እና በተለይም ተተኪ ትውልድ ላይ በእጅጉ መስራት እንደሚገባ ገልፀዋል። በመጨረሻም ሰርሆተ ሕዝብ ከሆነ በኋላ በብስራተ ገብርኤል ቤተ ክርስትያን አዳራሽ ጉባኤው ቀጥሎ ውሏል።

ምዕመናን አስቀድመው ቦታቸውን የያዙ ሲሆን አባቶች ካህናት ሲገቡ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች በመዝሙር ፣ በዕልልታ እና በጭብጨባ በመቀበል ለአባቶች ካህናት ያላቸውን አክብሮት ገልፀዋል።በተጨማሪ ዲያቆን ዘካርያስ እና ዘማሪ መንግስቱ ወቅቱን የተመለከቱ መዝሙራትን በማቅረብ በዓሉን አድምቀውታል።  በዚሁ ጉባኤ በUN የኢትዮጵያ አምባሳደር ታዬ አጽቀ ስላሴ ተገኝተዋል። የአዘጋጅ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ወንድም አገኘሁ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት አስተላልፈዋል። አክለውም ይህንን የአባቶች አንድነት እንዲመጣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ላደረጉት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አመስግነዋል። በመቀጠል ንግግር ያደረጉት አምባሳደር ታዬ አጽቀ ስላሴ ሲሆኑ የምስጋና መልዕክቱ በአግባቡና በስርዓቱ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ እንደሚያስተላልፉ ቃል ገብተዋል። በተጨማሪም ቤተ ክርስትያን ለአገር አንድነትና ሰላም ያደረገችው አስተዋፅኦ ከፍተኛ መሆኑን ገልፀዋል። በመቀጠል የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች የደብረ ገነት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስትያን ተወካይ ወጣት መኮንን ቤተ ክርስትያን አፍሪካን አሜሪካን (African American) በእንግሊዝኛ ቋንቋ በማስተማር እንድትደርስላቸው ተማፅነዋል። ከዚህ በኋላ የእንግሊዝኛ ተናጋሪዎች የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች መዝሙር በእንግሊዝኛ፤በግዕዝ፤በአማርኛ አቅርበዋል።

በተጨማሪ የኒውዮርክ ደብረ ብርሃን ቅድስት ስላሴ (በሰሜን አሜሪካ የመጀመርያው የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ) አስተዳዳሪ መጋቤ አእላፍ ኤፍሬም የደስታ መግለጫ መልእክት አስተላልፈዋል። በተመሳሳይ መልኩ ሌሎች የቤተ ክርስትያን አስተዳዳሪ አባቶች ካህናት የተሰማቸውን የደስታ መግለጫ  መልእክት አቅርበዋል።ቀጥሎም በሰሜን አሜሪካ የማህበረ ቅዱሳን የኒውዮርክ ግንኙነት ጣብያ ሰብሳቢ ዲያቆን ዶክተር ምሕረተአብ “ዕርቅ የሚያደርጉ ብፁዓን ናቸው፤ እነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና“ (ማቴ ፭፥፱) በሚል መነሻ ርዕስ ማህበሩ በአባቶች አንድነት የተሰማውን ደስታ ገልፀዋል። የማህበሩ አባላትም ልጆችን በማስተማር እና መዝሙራትን በማቕረብ ተሳትፈዋል። በመጨረሻም የአዘጋጅ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ወንድም አገኘሁ ይህንን ጉባኤ ያዘጋጁ ከ ፲፩ አብያተ ክርስትያናት የተውጣጡና ከማህበረ ቅዱሳን የተወከሉ ፪ አባላት በድምሩ ፳፬ አባላት እና በአጠቃላይ ይህንን ጉባኤ እንዲሳካ ለደከሙት ሁሉ ምስጋና በማቅረብ በአባቶች ካህናት ጸሎትና ቡራኬ የጉባኤው ፍጻሜ ሁኗል።

በማኅበረ ቅዱሳን የሰሜን አሜሪካ ማእከል የኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ 2ተኛውን ሐዊረ ሕይወት በተሳካ ሁኔታ አካሄደ

በማኅበረ ቅዱሳን የሰሜን አሜሪካ ማእከል  የኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ 2ተኛውን ሐዊረ ሕይወት በተሳካ ሁኔታ አካሄደ::

ግንኙነት ጣቢያው መነሻውን ከኢንዲያና ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በማድረግ ኦሃዮ ኮሎምበስ ወደሚገኘው የደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ቅዳሜ ፣ ጥቅምት 10 ቀን 2011 ዓ. ም በኢንዲያና ዙሪያ የሚገኙ ከ70 በላይ ምዕመናንን ያሳተፈ መንፈሳዊ ጉዞ አካሂዷል።

የጉዞው ተሳታፊዎች በደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቅጽር መገኘት የጀመሩት ከጠዋቱ 6:00 AM ሰዓት ቀደም ብለው ሲሆን ሁሉም ተሳታፊዎች በየተመደቡበት አውቶብስ ወይም ቫን መሳፈራቸው እንደተረጋገጠ በኢንዲያና ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ሰላም ቀሲስ ንጉሤ ጸሎት ከተደረገ በኋላ ጉዞው ተጀምሯል። 3 ሰዓታት በፈጀው ጉዞ ተጓዦቹን በሐዋርያትና በቅዱሳን ስም በቡድን በመመደብ የመንፈሳዊ ጥያቄና መልስ ውድድር እንዲያደርጉ የተደረገ ሲሆን በጉዞው መጀመሪያና መጨረሻ በጋራ በመዘመር ጉዞው ልዩ መንፈሳዊ ድባብ እንዲኖረው ሆኗል።

ተጉዋዦቹ ኦሃዮ ደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ሲደርሱ በደብሩ ካህናትና ምዕመናን አቀባበል ከተደረገላቸው በኋላ መርሐ ግብሩ በካናቱ መሪነት በጸሎት ተከፍቷል። በመቀጠልም የቁርስ መስተንግዶ በደብሩ ምዕመናን ተደርጎ ለእለቱ የተዘጋጁት መርሐ ግብራት  ቀጥለዋል። በእለቱ መልአከ አርያም ቀሲስ ብርሃኑ ጎበና መስማትንስ ስላንተ ቀድሞ በጆሮዬ ሰምቼ ነበር፤ አሁን ግን ዓይኔ አየችህ በሚል ኃይለ ቃል መነሻነት እንዲሁም የደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ሰላም ቀሲስ ያሬድ ገብረ መድኅን ንሥሐ  በሚል ርዕስ ትምህርተ ወንጌል የሰጡ ሲሆን ጸሐፌ ትዕዛዝ መምህር ታዴዎስ ግርማ ደግሞ ሰፊ የዝማሬ አገልግሎት ሰጥተዋል ። እንዲሁም ከምዕመናን ለተነሱ ጥያቄዎች በመምህራኑ ምላሽ ተሰጥቷል።

በእለቱ የኢንዲያና ደብረ ሰላም  ቅዱስ ሚካኤል እና ደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል አብያተ ክርስቲያናት ሰንበት ትምህርት ቤቶች በጋራ መዝሙራትን ያቀረቡ ሲሆን ሦስት ታዳጊ ልጆች ደግሞ አባታችን በሰማያት ላይ ያለህ የሚለውን የበገና መዝሙር በጋራ አቅርበዋል።

በጉባኤው ከቀረቡት መርሐ ግብራት  የተሳታፊቹን ልዩ ትኩረት ያገኘው ዶ/ር በላይነህና ዲ/ን ፍሥሐ ያቀረቡት በማኅበረ  ቅዱሳን  ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስተባበሪያ የሐዋርያዊ  አገልግሎት ማስፋፊያ ዋና ክፍል የተዘጋጀውን የአዳ አማንያን ጥምቀት ሪፖርት ፈተናዎችና  ቀጣይ ሥራዎች  የተመለከተ በቪዲዮ የታገዘ ገለጻ ሲሆን በተሳታፊዎቹ ዘንድ ከፍተኛ ቁጭትን አሳድሯል። እንዲሁም የተወሰኑ ምዕመናንም ይህን እንቅስቃሴ ለመደገፍ ቃል እንዲገቡ ምክንያት ሆኗል።

በኢንዲያናና አካባቢው የሚገኙ ምዕመናን ሰፊ ትምህርተ ወንጌል እንዲያገኙ ፣ ከተዘጋጀው የምክረ አበው እና ሰፊ የዝማሬ አገልግሎት በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲበረቱ እንዲሁም ለጥያቄዎቻቸው መልስ እንዲያገኙ ታስቦ በተዘጋጀው በዚህ ሐዊረ ሕይወት የተሳተፉት ምዕመናን በመንፈሳዊ ጉዞው መደሰታቸውን ገልጸዋል። እንዲሁም ለኦሃዮ ደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን $1,156.00 ዶላር መብዐ ሰብስበው ሰጥተዋል።

ለሐዊረ ሕይወቱ መሳካት የኢንዲያና ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ምዕመናንን በመቀስቀስ ፣ የትራንስፖርትና የመሳሰሉትን ለጉዞ አስፈላጊ ነገሮች በማፈላለግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረጉ ሲሆን የኦሃዮ ደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያንም እንዲሁ ከአስተዳዳሪው ጀምሮ ሰበካ ጉባኤውና ምዕመናንኑ ለተጓዦቹ የቁርስና ምሳ መስተንዶ በማድረግ ፣ በደብሩ የተጋጀውን የ2011ዓ.ም ቀን መቁጠሪያ በነጻ በማደል እንዲሁም መርሐ ግብሩ የተሳካ እንዲሆን አስፈላጊውን ሁሉ በማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርገዋል።

በመጨረሻም ተጉዋዦቹን መርተው የሄዱት የኢንዲያና ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ሰላም ቀሲስ ንጉሤ ገብሬ ለሐዊረ ሕይወት አስተባባሪዎቹ የማኅበረ ቅዱሳን ኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ ፣ ለአስተናጋጁ ደብር ኦሃዮ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ፣ ለሁለቱ ሰንበት ትምህርት ቤቶች እንዲሁም በጉባኤው ላይ ለተገኙት ካህናት መዘምራን እና ምዕመናን ምስጋና አቅርበዋል። የማኅበረ ቅዱሳን ኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ ሰብሳቢ ዶ/ር ዓለማየሁ በበኩላቸው ለጉዞው መሳካት አስተዋጽኦ ላደረጉት ካህናት ፣ አድባራት ፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች እንዲሁም ተሳታፊ ምዕመናን ምስጋና አቅርበው መርሐ ግብሩ 5፡30 PM ላይ በጸሎት ተደምድሟል። ተጉዋዦቹም እየዘመሩ ወደ ኢንዲያና በሰላም ተመልሰዋል።

Ethiopia: the Land with an immense Literary Heritage

“Ethiopia: the Land with an immense Literary Heritage”

Expression of thoughts, actions, wars, victory, belief, etc. in written form during the classical era reveals human civilization. Ethiopia, having immense literary heritages for over two millennia, is the nation in Africa that possesses the second largest literary heritage next to Egypt. Ge‘ez (classical Ethiopic) is a language which serves as a medium for conveying this literary heritage. As a spoken language during and after the Axumite time, Ge‘ez plays a prominent role in socio-economic, and religio-cultural settings of the country. The “Garima Gospel”, which is the oldest existent codex in the Christian world (composed 4th – 6th cent. A.D.) is written in Ge‘ez. There are hundreds of thousands of manuscripts in Ethiopia composed in this language and deposited in different monastic archives of the country.

The golden age of Ge‘ez literature, as most scholars agree, is between the 14th to 18th centuries. Most of the works are translations from Greek, Syriac and mostly Arabic. There are a number of indigenous texts composed by Ethiopians and the list of the most influential authors include St. Yared, Abba Giyorgis of Gasicha, Abba Baheri, Emperor Zera Yaqob, Arke Sellus, and Retu’a Haymanot. The literary genre of Ethiopic literature is diverse including: biblical and religious texts, hagiographies, homiliaries, hymnodic and liturgical texts, prayer books, royal chronicles, esoteric traditions, linguistic narratives, etc.

The current conference is the Second International Conference of Ethiopian Church Studies, dedicated to discuss different topics under the theme: “Ge‘ez Literature and Manuscript Traditions in Ethiopia”. This conference is a continuation of the conference held in Lund (Sweden) titled “Ethiopian Ecclesiastical Heritage”, September 2-3, 2017, convened at Lund University. There are three keynote speakers in this conference and we have a privilege to have Prof. Getatchew Haile, the leading scholar on Ethiopian Studies, as one amongst them. We have received a large number of submissions but selected 13 papers. The papers cover the topics on biblical translations, the art of Ethiopic poetry (Qene), the significance of Ge‘ez hagiographies for the reconstruction of Ethiopian history, medicinal texts, Yaredic chanting book (Deggwa), the use of modern technology for manuscripts studies, etc. Now is the time to give due attention to explore and study Ethiopian literary heritages and to draw the attention of the stakeholders for preservation and conservation of Ethiopian manuscripts.

We, the organizers of the Second International Conference would like to thank all paper presenters and collaborators who made this conference possible. We are grateful for Mahibere Kidusan USA and Europe centers, and special thanks goes to Mahibere Kidusan Atlanta Sub-Center for their significant role in the process of organizing the conference.

May the Almighty God help us keep our literary heritage!

ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ በሰሜን አሜሪካ ሊካሄድ መሆኑ ተገለጸ

  ቀሲስ ሳሙኤል ተስፋዬ መስከረም 23 ቀን 2011/October 3,2018                        

ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ በሰሜን አሜሪካ ሊካሄድ መሆኑ ተገለጸ ::

የግዕዝ ሥነ ጽሑፍና የብራና ቅርሶች በኢትዮጵያ”  በሚል መሪ ቃል ሁለተኛው  ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ በማኅበረ ቅዱሳን  የአሜሪካና  የአውሮፓ  ንዑሳን ማዕከላት አስተባባሪነት ከጥቅምት ፲-፲፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም/October 20-21/2018  በሰሜን አሜሪካ፣  አትላንታ  ጆርጂያ በ 6202 Memorial Drive Stone Mountain, GA 30083  ሊካሄድ መሆኑ ተገለጸ፡፡

የዓለም አቀፍ ጥናት ጉባኤ ኮሚቴ  ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ተፈራ (Ludwig Maximilian University, Munich, Germany) እና የኮሚቴ  አባልና የዐውደ ጥናቱ  አስተባባሪ ዶ/ር ፍሬሕይወት ወንድሙ (Wichita State University, USA) በጋራ  እንደገለጹልን  ለሁለተኛ ጊዜ በአሜሪካ አትላንታ ጆርጂያ ከተማ የሚካሄደው  ዓለም አቀፍ የጥናት ጉባኤ፤  የመጀመሪያው  ዓለም አቀፍ ዐውደ ጥናት ጉባኤ በማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል  አስተባባሪነት  በስዊድን  ሉንድ  ከተማ በተካሄደበት ወቅት  ከነበረው የዐውደ ጥናቱ  ፋይዳ፣ ቀጣይነትና አቅጣጫዎች በመነሳት  ሁለተኛው  ዐውደ ጥናት በሰሜን አሜሪካ  እንዲሆን መወሰኑን ገልጸዋል፡፡  በተጨማሪም የዐውደ ጥናቱ ዋነኛ ዓላማም  የኢ/ኦ/ተ/ ቤተክርስቲያንን በዓለም አቀፍ መድረክ ማስተዋወቅ ፣ በርካታ ምሥጢራትን ይዘው የሚገኙ  የቤተ ክርስቲያን   ቅርሶቻችን ላይ ጥናትና ምርምር ማድረግ፣ ጥናትና ምርምር  የተደረገባቸውንም  ቅርሶች   በማወያየት ሀብቶቹ የሚጠበቁበትንና  ለተሻለ አገልግሎት የሚበቁበትን  ሁኔታ ማመቻቸት እንደሆነ ገልጸውናል፡፡

የጥናቶቹን  ይዘትና  ማቅረቢያ  ቋንቋ በተመለከተ ለኮሚቴው ተወካዮች ላቀረብነው ጥያቄ፤  ጥናቶቹ  በአማርኛና በእንግሊዝኛ ቋንቋዎች የሚቀርቡ ሲሆኑ  በጉባኤው ላይ የሚቀርቡ ጥናታዊ ጽሑፎች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከቱ ሆነው፤ የአንድምታ  ትርጓሜ፣ገድላት፣ድርሳናት፣መልክአ መልኮች፣ቅኔ ፣ዜማ ፣የብራና ጽሑፎች  ፣የመድኃኒት ይዘት ያላቸው ጥቅልል ጽሑፎች፣በብራና ውስጥ የሚገኙ ሥዕሎችና በዚህ ዝርዝር ላይ ያልተካተቱ ሌሎች ከጉባኤው ዓላማ ጋር የሚሄዱ ርእሶችም  እንደሚቅቡ  ገልጸውልናል፡፡

 

”ጥናት አቅራቢዎቹ   በቤተክርስቲያናችን ቅርሶች ዙሪያ ጥናታዊ ምርምር የሚያካሂዱ ኢትዮጵያውያንና የውጭ ዜጎች ሲሆኑ  የጥናት አጠቃሎአቸውን  ኮሚቴው ባስቀመጠው የመገምገሚያ  መስፈርት መሰረት ነጥብ በመስጠት   የተሻለ ነጥብ ያመጡት 13 ጥናቶች ለጉባኤው ሊቀርቡ ዝግጁዎች ናቸው፡፡ የተመረጡት የጽሑፍ አጠቃሎዎች በመጽሔት መልክ ታትመው በጉባኤው የሚሠራጩና በጉባኤው ላይ ቀርበው ውይይት የተደረገባቸውና መመዘኛውን የሚያሟሉ የጥናት ወረቀቶች ደግሞ  በ“የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት መጽሔት” (Journal of Ethiopian Church Studies) እንዲታተሙ ይላካሉ፡፡” ሲሉም አስተባባሪዎቹ ገልጸውልናል፡፡

የጉባኤው አዘጋጅ ኮሚቴ  አባላት13 ሲሆኑ  በአውሮፓ፣በአሜሪካና ካናዳ የሚኖሩ የማኀበረ ቅዱሳን አባላትና ደጋፊዎች የሆኑ በተለያዩ  ዩኒቨርሲቲዎች በማስተማርና ጥናትና ምርምር በማድረግ ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንናቸው፡፡ በተጨማሪም  የውጭ ሃገር ዜጎች የሆኑ በኢትዮጵያ  ቤተክርስቲያን ታሪክ፣ ዜማና ብራና መጻሕፍት ላይ ምርምር እያደረጉ የሚገኙ  ምሁራን በማማከር ስራዎች እየረዱ እነደሆነም ለመረዳት ችለናል፡፡

 

በዐውደ ጥናቱ ሦስት ቁልፍ ተናጋሪዎች (Keynote Speakers) ሲኖሩ እነዚህም፡-

1.ሊቀ ካህናት ኃይለ ሥላሴ ዓለማየሁ – የዴንቨር ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም የኢ.ኦ.ተ. ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ፣ ሰሜን አሜሪካ፡፡

2.ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ – ሒል ሙዚየም (HMML)፣ ኮሌጅቪል፤ ሰሜን አሜሪካ፡፡

3.ፕሮፌሰር ስቲቭ ዴላማርተር – ጆርጅ  ፎክስ ዩኒቨርሲቲ፣  ሰሜን አሜሪካ  መሆናቸው ተገልጿል፡፡